በኮንሶ ዞን የከና ወረዳ -ደበና -ከመሌ የ 7 ነጥብ 54 ኪሎ ሜትር መንገድ ግንባታ በይፋ ተጀመረ

በኮንሶ ዞን የከና ወረዳ -ደበና -ከመሌ የ 7 ነጥብ 54 ኪሎ ሜትር መንገድ ግንባታ በይፋ ተጀመረ

ሀዋሳ፡ ነሐሴ 05/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) በ40 ሚሊየን ብር ወጪ የሚገነባው የኮንሶ ዞን ከና ወረዳ -ደበና -ከመሌ የ 7 ነጥብ 54 ኪሎ ሜትር መንገድ ግንባታ በይፋ ተጀምሯል።

‎የመንገድ ግንባታው መጀመር ያመረቱትን ምርት ለገበያ ከማቅረብ ባሻገር የህዝብ ለህዝብ ትስስርን በማጠናከር ያለው ፋይዳ ላቅ ያለ መሆኑን ነዋሪዎች አረጋግጠዋል።

‎በኮንሶ ዞን የከና ወረዳ ነዋሪዎች መካከል አቶ ከፋይ ገብሬና ገዛኸኝ ገሌቦ እንዳሉት የዘመናት ጥያቄ የነበረውን የመንገድ መሠረተ ልማት ምላሽ በመስጠት መንግስት ያደረገው ጥረት የሚደነቅ መሆኑን ጠቁመዋል።

‎የመንገድ መሠረተ ልማቱ ሲጠናቀቅ ያመረትነውን ምርት ገበያ በማድረስ ተጠቃሚ ከመሆናቸውም ባሻገር የህዝብ ለህዝ ትስስርን እንደሚያጠናክር ነዋሪዎቹ ገልፀዋል ።

‎በዚህ ወቅት መልዕክት ያስተላለፉት የከና ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ ካርሾ ገዴኖ፥ የገጠር የመንገድ ትስስር ለምግብ ዋስትና ፕሮግራም እና ለአከባቢው ነዋሪ ብሎም ለአርሶአደሩ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ አለው ብለዋል ።

‎መንገዱ በርካታ ቀበሌያትን በማስተሳሰር በአከባቢው ለውጥ እንዲመዘገብ የሚያደርግ በመሆኑ ህብረተሰቡ ለመንገዱ ግንባታ የበኩሉን እንዲወጣ ጥሪ ያስተላለፉት ደግሞ የኮንሶ ዞን መንገድና ትራንስፖርት ልማት መምሪያ ኃላፊ አቶ ሰለሞን ካሊታ ናቸው ።

‎የኮንሶ ዞን ም/አስተዳዳሪ እና የግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ ጉራሾ ጎስኬ የመንገድ ጥያቄ ረጅም ጊዜ የመልካም አስተዳደር ጥያቄ እንደነበር አስታውሰው፥ መንግስት ባደረገው ጥረት የህዝቡን የመሠረተ ልማት ጥያቄ ደረጃ በደረጃ በመመለሱ ደስተኛ ሆነናል ብለዋል።

‎የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ትራንስፖርትና መንገድ ልማት ቢሮ ምክትል ኃላፊና የትራንስፖርት ዘርፍ ኃላፊ ብርሃኑ ጌቦ (ዶ/ር) ቢሮው ከአለም ባንክ ጋር በመተባበር በ40 ሚሊየን ብር ወጪ የመንገድ ግንባታውን መጀመሩን ተናግረዋል።

‎ከዚህ ቀደም የተገነቡትን የማስተካከል እና 7 ነጥብ 54 ኪሎ ሜትር ጠረጋ እንደሚደረግ ጠቁመው፥ ይህም ለወረዳው ያለው ፋይዳ ዘርፈ ብዙ እንደሆነ ተናግረዋል።

‎ዘጋቢ፡ ተመኙህ ገረሱ – ከአርባምንጭ ጣቢያችን