በጌዴኦ ዞን የጎብኚዎች ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ መምጣቱ ተገለጸ
ሀዋሳ፡ ሐምሌ 29/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) የጌዴኦ ዞንን የሚጎበኙ ሰዎች ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ መምጣቱን የዞኑ ባህልና ቱሪዝም መምሪያ አስታወቀ።
የጌዴኦ ዞን ባህልና ቱሪዝም መምሪያ ኃላፊ አቶ ደርቤ ጂኖ በዞኑ ያለው መልከአ ምድርና በውስጡ ያለ የቱሪስት መዳረሻዎችን የተለያዩ አማራጮችን ተጠቅመው እያስተዋወቁ መሆናቸውን አስረድተዋል።
በማህበራዊ ገጾች፣ በተለያዩ ሚዲያዎችና በዌብ ሳይቶች የማስተዋወቅ ሥራ እየተሠራ ነው ያሉት ኃላፊው፥ የጌዴኦ መልከአ ምድር አያያዝ በዩኔስኮ የተመዘገበ መሆኑ፣ የቡና ቱሪዝም እና የደራሮ በዓልም ለዘርፉ ዕድገት አዎንታዊ አስተዋህጾ አድርገዋል ብለዋል።
ከጌዴኦ መልከአ ምድር አያያዝን ጨምሮ በርካታ የቱሪስት መዳረሻ የሚሆኑ ቦታዎች መኖራቸው ጠቁመው፥ ከነዚህም መካከል ትክል ድንጋዮች፣ ፋፋቴዎች፣ ራኮና ባሪቻ ተራራዎች እና ዋሻዎችን ለአብነት አንስተዋል።
በዞኑ ያለው የሰላም አየር፣ የደራሮ በዓል አከባበር፣ የማህበረሰቡ የእንግዳ አቀባባል፣ ጥምር እርሻና ባህላዊ የምግብ ዝግጅት የቱሪዝም ፍሰት እንዲጨምር በማድረግ ዘርፉ እንዲነቃቃ እያደረጉ ያሉ ጉዳዮች መሆናቸውን አቶ ደርቤ አስረድተዋል።
ከመጋቢት ወር ጀምሮ የቅርስ አስተዳደር ጽህፈት ቤት በዞኑ ተከፍቷል ያሉት ኃላፊው፥ ቅርሶችን የመንከባከብ፣ የመጠበቅና የማልማት ሥራዎችን ልዩ ትኩረት ሰጥቶ በመደራጀት እንደሚሠሩ አብራርተዋል።
የቱሪዝም መዳረሻዎች ላይ የመሠረተ ልማት ዝርጋታ ጉዳይን ጨምሮ መጸዳጃ ቤቶች፣ ሆቴሎች እና ሌሎች አገልግሎቶችን ለማሟላት የግሉ ዘርፍና የመንግሥት ልዩ ትኩረት የሚጠይቅ ተግባር መሆኑን ተናግረዋል።
በ2018 በጀት ዓመት ላይ ዘርፉን ማነቃቃት ከባህላዊ አስተዳደር ጨምሮ በዞኑ የቱሪስት መዳረሻዎችን በተለያዩ አማራጮች ለማስተዋውቅ ከሁሉም መዋቅሮች ጋር ተቀናጅተው በትኩረት እንደሚሠሩ አስገንዝበዋል።
ዘጋቢ፡ ተስፋዬ ጎበና – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን
More Stories
የማኑፋክቸሪንግ ዘርፉን በተገቢ መደገፍና ማበረታታት ለሃገር ኢክኖሚ እድገት ያለው ሚና ከፍተኛ መሆኑን ተገለጸ
በጎፋ ዞን በተጠናቀቀው የበጀት ዓመት 1 ሺህ 830 ቶን ቡና ለማዕከላዊ ገበያ መቅረቡ ተገለጸ
በመኸር እርሻ ከ1 ነጥብ 6 ሚሊዮን በላይ ኩንታል ምርት ይጠበቃል – የጌዴኦ ዞን ግብርና መምሪያ