የሥነ ምግባር መጓደል ለበርካታ ቀውሶች እንደሚዳርግ ተገለፀ
ሀዋሳ፡ ሰኔ 01/2015 ዓ.ም (ደሬቴድ) የሥነ ምግባር መጓደል ለበርካታ ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ቀውስ እንደሚዳርግ ተገለፀ፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ሥነ ምግባርና ፀረ-ሙስና ኮሚሽን በአስተዳደሩ ሥር ከሚገኙ የሀይማኖት አባቶች እና አባገዳዎች ጋር በሥነ ምግባር፣ በሌብነት ጠንቆች እና በሰላምና ፀጥታ ጉዳዮች ዙሪያ ውይይት እያደረገ ነው።
የአስተዳደሩ ሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን ኮሚሽነር ጀማል ረዲ እንደገለፁት ሌብነት የአገርን ኢኮኖሚ ከማናጋቱ ባሻገር በከፍተኛ ሁኔታ ሰላምን ያናጋል።
ሌብነትን የሚጸየፍ ትውልድ በመገንባት ረገድ የሀይማኖት አባቶች ኃላፊነታቸውን በተገቢው ሊወጡ እንደሚገባ ኮሚሽነሩ ተናግረዋል።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ አቶ ጃንጥራር አባይ በበኩላቸው ኢትዮጵያ የእምነት ሀገር መሆኗን ገልጸዋል።
ሆኖም ግን አሁን አሁን የሥነ ምግባር መጓደል እና ሌብነት በቤተእምነቶች ጭምር እየተንሰራፋ ስለሆነ የእምነት አባቶች በሥነ ምግባር የታነጸና ከክፉ ድርጊት የራቀ ትውልድ እንዲገነባ አበክረው ሊሰሩ ይገባል ሲሉም አስገንዝበዋል።
ሌብነት እየነገሰ ሲመጣ መንግስታት ሥርዓት አልባ ይሆናሉ ያሉት አቶ ጃንጥራር አባይ የሥነ ምግባር መጓደልንና ሌብነትን በጋራ መከላከል ይገባልም ብለዋል።
የሥነ ምግባር መጓደል ለሌብነት መስፋፋት፣ ለአድሎአዊ አሠራር፣ ለአሠራር ጥሰት፣ ብሄርተኝነትን ለማቀንቀን እና መሰል ችግሮች መስፋፋት መንስኤ እንደሚሆንም አስታውቀዋል።
ችግሮቹን መፍታት በሚቻልባቸው ጉዳዮች ዙሪያም ከሃይማኖት አባቶች ጋር ውይይት ተደርጓል።
ዘጋቢ፡ ጌታሁን አንጭሶ

More Stories
ህዝበ ክርስቲያኑ የ2019 ዓ.ም የእንቁጣጣሽ በዓልን በሚያከብርበት ወቅት አቅመ ደካሞችን በመደገፍ ሊሆን እንደሚገባ የጠምባሮ ልዩ ወረዳ የሀይማኖት አባቶች ተናገሩ
የ2018 በጀት ዓመት ኢትዮጵያ በተለያዩ ዘርፎች ታላላቅ ስኬቶችን ያስመዘገበችበት እና የዲጂታል ሽግግር የሉዓላዊነቷ ምሰሶ መሆን የቻለችበት አመት መሆኑን አቶ አልማው ዘውዴ ገለፁ
ጳጕሜን 5 “የነገው ቀን” በኮሬ ዞን በልዩ ልዩ ዝግጅቶች እየተከበረ ነው