የፍትሕ ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ አቶ አለምአንተ አግደው በአሜሪካ የዓለም አቀፉ ናርኮቲክስ እና የሕግ አስፈጻሚ ድርጅት ዳይሬክተር የሌና ዘርኡ ጋር ተወያዩ

የፍትሕ ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ አቶ አለምአንተ አግደው በአሜሪካ የዓለም አቀፉ ናርኮቲክስ እና የሕግ አስፈጻሚ ድርጅት ዳይሬክተር የሌና ዘርኡ ጋር ተወያዩ

ሀዋሳ፡ ሰኔ 01/2015 ዓ.ም (ደሬቴድ) የፍትሕ ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ አቶ አለምአንተ አግደው በአሜሪካ የዓለም አቀፉ ናርኮቲክስ እና የሕግ አስፈጻሚ ድርጅት ዳይሬክተር የሌና ዘርኡ ጋር ተወያይተዋል፡፡

በውይይታቸውም በሂደት ላይ በሚገኘው ሀገራዊ የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲ ዝግጅት እንቅስቃሴዎች እና በድርጅቱ ትብብር እየተከናዎኑ በሚገኙና ወደፊት በጋራ ትብብር ሊከናዎኑ በሚገባቸው የተለያዩ ጉዳዮች ዙሪያ መክረዋል፡፡

ሚኒስትር ዴኤታ አቶ አለምአንተ አግደው፤ ድርጅቱ ትብብር እያደረገ የሚገኝበት ሀገራዊ የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲ ዝግጅት ሂደት እና ተያያዥ ጉዳዮች ያሉበትን ደረጃ በመግለጽ ምስጋና አቅርበዋል፡፡

የፍትሕ ሚኒስቴር በሀገሪቱ የሕግ የበላይነት እና መልካም አስተዳደር እንዲሰፍን ከማድረግ ጋር ቀጥተኛ ቁርኝት ያላቸው በርካታ ተግባርና ኃላፊነቶች በሕግ የተሰጡት መሆኑን ግምት ውስጥ በማስገባት ድርጅቱ ከመስሪያ ቤቱ ጋር በትብብር የሚሰራቸውን ስራዎች በቀጣይ በማጠናከርና የበለጠ በማስፋት እንደሚቀጥል ያላቸውን እምነት ገልፀዋል፡፡

የሌና ዘርኡ በበኩላቸው ድርጅቱ በተለይም በሀገራዊ የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲ ዝግጅት ሂደቱ ላይ እስካሁን ትብብር ሲያደርግ መቆየቱን አውስተው ከዚሁ ጋር በተያያዘ በቀጣይ ድጋፍ የሚፈልጉ ጉዳዮች ተለይተው እና ዝርዝር ጉዳያቸው ተመልክቶ ቢቀርብ በትብብር ለመስራት አመቺነት እንደሚኖረው መግለፃቸውን ከፍትሕ ሚኒስቴር የተገኘ መረጃ ያመላክታል፡፡

ዳይሬክተሯ አክለውም ድርጅቱ ትብብሩን በዚሁ ረገድ አጠናክሮ እንደሚቀጥልና በሌሎች የትብብር ጉዳዮች ላይ በቀጣይ ትብብር በሚደረግበት ሁኔታ ላይ ከሚመለከታቸው ጋር በመነጋገር የሚቻለውን ሁሉ እንደሚያደርጉ ገልፀዋል።