በጤና ዘርፍ የተቀመጡ ግቦችን ለማሳካት ብቁ የሰው ሀይል ወሳኝ ሚና እንዳለው የጤና ሚኒስቴር ገለጸ

11ኛው ዓመታዊ የጤናው ዘርፍ ሀገር አቀፍ የሰው ሀብት ፎረም በአርባ ምንጭ እየተካሔደ ነው።

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ ሀላፊ አቶ እንዳሻው ሽብሩ በመክፈቻ ንግግራቸው እንዳሉት የዓለም ጤና ድርጅት ካስቀመጣቸው ዋና ዋና ግቦች አንዱ የሆነውን የሰው ሐብት ልማት ዘርፍ በማጠናከር ሩህሩሁ እና ተንከባካቢ ባለሙያ ለማብቀት እየተሰራ ነው።

በክልሉ ከ1 ሺ 200 ከፍተኛ ባለሙያዎችን በማሰልጠን ወደ ጤናው ሥራ እንደተሠማሩ ገልጸው የባለሙያዎችን ወቅቱ በሚፈልገው ሁኔታ ለማብቃት በየጊዜው እየተሠራ መሆኑንን የቢሮ ሀላፊ ተናግረዋል።

የኢፌዴሪ ጤና ሚኒስቴር ሚኒስቴር ዴኤታ ወ/ሮ ሳህረላ አብዱላህ ብቁ እና ሙያዊ ስነ ምግባር የተላበሰ የሰው ሀይል በማሰልጠንና በመቅጠር ውጤታማነትን መሠረት ያደረገ የማበረታቻ እና የማቆያ ሥራ በቀጣይ በትኩረት ለመሥራት መታቀዱን አብራርተዋል።

እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር በ2030 ላይ እንዲሳኩ የታቀዱ ዓለም ዓቀፍ እና አገር አቀፍ ግቦችን ለማሳካት የሰው ሀብት ስትራቴጂክ ዕቅድ በማዘጋጀት ለውጤታማነት በትኩረት ይሠራልም ብለዋል ሚኒስቴር ዴኤታዋ።

በምክክሩ መድረኩ ከክልል ጤና ቢሮዎች የሰው ሐብት ልማት አስተዳደር ፣የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተወካዮች ፣ ከሙያ ማህበራት እና አጋር አካላት የተገኙ ባለ ድርሻዎች ተሳታፊ ናቸው።

ዘጋቢ: ወ/ገብርኤል ላቀው -ከአርባ ምንጭ ጣቢያችን