ዩኒቨርሲቲዉ የጉራጊኛ ቋንቋ፣ ባህል እና ሀገር በቀል እዉቀትን ማልማት ላይ ትኩረት ያደረገ ስልጠና ለሚዲያ እና ኮሙኒኬሽን ባለሙያዎች እና አመራሮች ሰጥቷል።
ስልጠናዉን በንግግር ያስጀመሩት የዩኒቨርሲቲዉ የአካዳሚክ ጉዳዮች ምክትል ፕሬዝዳንት ዶ/ር ሀብቴ ዱላ፤ ኢትዮጵያ በአህጉርም ሆነ በአለም አቀፍ ደረጃ የምትታወቅበት የበርካታ እሴቶች ባለቤት ናት ብለዋል።
በመሆኑም እነዚህ እሴቶች ቀጣይነት እንዲኖራቸዉ የአሁኑ ትዉልድ ትልቅ ሀላፊነት እንዳለበትም አመላክተዋል።
ሚዲያዎች በህብረተሰቡ ላይ ትልቅ ተጽእኖ የመፍጠር አቅም አላቸዉ ያሉት ስልጠናዉን የሰጡት በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የማህበራዊ ሳይንስ እና ስነ ሰብ ኮሌጅ የሶሻል አንትሮፖሎጂ ትምህርት ክፍል መምህርና ተመራማሪ ዶ/ር አራጌ ይመር ናቸዉ።
በመሆኑም የሚዲያ ባለሙያዎች በቋንቋ እና ባህል ላይ ያገኙትን መልሰዉ መንገር ሳይሆን ጥንቃቄ በተሞላበት መንገድ መስራት ይጠበቅባቸዋልም ነው ያሉት።
የወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ የቋንቋ፣ ባህልና ሃገር በቀል እውቀቶች ልማት ማእከል ዳይሬክተር ረዳት ፕሮፌሰር ካሚል ኑረዲን በበኩላቸው፤ የጉራጊኛ ቋንቋ እንዲበለፅግ፣ አካባቢን እንዲያስተዋውቅና አለምአቀፋዊ እውቅናን እንዲያገኝ ሚዲያና የሚዲያ አካላት ፈር ቀዳጅ በመሆናቸው ይህን ታሳቢ በማድረግ ዩኒቨርሲቲው ጅምር ተግባሮችን እያከናወነ እንደሚገኝ አብራርተዋል።
የስልጠናው ተሳታፊዎች በሰጡት አስተያየት፤ የጉራጊኛ ቋንቋ የሚዲያ ቋንቋ ሆኖ እንዲያገለግል እየተደረገ ያለውን በማጠናከር በቀጣይ ቋንቋውን ይበልጥ ለማልማት በትኩረት መሰራት አለበትም ብለዋል።
በስልጠናው መድረክ የጉራጊኛ ቋንቋ ፊደላት፣ መማሪያ፣ ማስተማሪያና መፃፊያ መተግበሪያ ለሰልጣኞች ትውውቅ የተደረገ ሲሆን የዘዬዎች አጠቃቀምም የልምድ ልውውጥ ተደርጓል።
በዚህ ለሁለት ቀናት በተሰጠው ስልጠና ላይ በጉራጊኛ ቋንቋ የሚሰሩ የሚዲያ እና ኮሙኒኬሽን ባለሙያዎች እና አመራሮች ተሳትፈዋል።
ዘጋቢ፡ ረድኤት እግዜሩ – ከወልቂጤ ጣቢያችን
More Stories
የኢፌዲሪ ውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር የአፍሪካ ቀንድ ዘላቂ የከርሰ ምድር ውሃ ፕሮጀክት ከ82 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ በማድረግ በጉራጌ ዞን ምሁር አክሊል ወረዳ መቆርቆር ቀበሌ ያስገነባው የንጹህ መጠ ውሃ ፕሮጀክት ተመርቆ ለአገልግሎት ክፍት ሆነ
የኡዱሂያ የዕርድ ስርዓት….የአብሮነት ነፀብራቅ
በቅርቡ በሚሰጠው የ6ኛ እና የ8ኛ ክልላዊ ፈተና ላይ ከ53 ሺህ በላይ ተማሪዎች ለፈተና እንደሚቀርቡ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የሀዲያ ዞን ትምህርት መመሪያ አስታወቀ