የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ትምህርት ቢሮ የትምህርት ጥራትን ለማስጠበቅ 7 ሺህ 321 ለሚሆኑ መምህራንና የትምህርት አመራር የብቃት ማረጋገጫ ፈተና እየሰጠ ነው – የክልሉ ትምህርት ቢሮ

ሀዋሳ፡ ግንቦት 23/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ትምህርት ቢሮ የትምህርት ጥራትን ለማስጠበቅ 7 ሺህ 321 ለሚሆኑ መምህራንና የትምህርት አመራር የብቃት ማረጋገጫ ፈተና እየሰጠ እንደሚገኝ የክልሉ ትምህርት ቢሮ አስታዉቋል።

ይህ የፈተና ምዘና መምህራንን ከዘመኑ ቴክኖሎጂ ጋር እንዲጓዙ የሚያስችላቸዉ መሆኑን የጋሞ ዞን ትምህርት መምሪያ ገልጿል።

በሃገሪቱ የሚስተዋለዉን የትምህርት ስብራት ለመጠገን በሚደረገው ጥረት ለመምህራን የብቃት ማረጋገጫ ፈተና በአርባምንጭ ከተማ እየተሰጠ ይገኛል።

በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ትምህርት ቢሮ በክልል ደረጃ 7321 ለሚሆኑ መምህራን እና ሱፐርቫይዘሮች ፈተና እየተሰጠ እንደሚገኝ የተናገሩት በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ትምህርት ቢሮ በካቢኔ ማዕረግ የጽህፈት ቤት ኃላፊ እና የፈተናዉ አስተባባሪ አቶ ተስፋዬ ደፋሩ ናቸው።

የሚሰጠዉ የምዘና ፈተና ብቻዉን በቂ እንዳልሆነና በቀጣይም በተማሪዎች ላይ እንደሚሰራ ገልፀው፤ የሚመለከታቸዉ ባለድርሻ አካላት የበኩላቸዉን አስተዋጽኦ እንዲያበረክቱ አስተባባሪዉ ጥሪ አአቅርበዋል።

በጋሞ ዞን በ3 ማዕከላት ከ2900 በላይ መምህራንና ሱፐርቫይዘሮች ፈተናዉ እየተሰጠ እንደሚገኝ የተናገሩት የጋሞ ዞን ትምህርት መምሪያ ኃላፊ አዲሱ አዳሙ(ዶ/ር) ናቸዉ።

ይህም በመማር ማስተማር ሂደት የትምህርት ጥራትን ለማስጠበቅ እና መምህራን ከዘመኑ ቴክኖሎጂዎች ጋር እንዲጓዙ ሚናዉ የላቀ እንደሆነም ሀላፊው አክለዉ ገልፀዋል።

ፈተናዉን ከተፈተኑት መምህራን መካከል መ/ር ቦንቃ ዎላዴ እና መ/ርት በቀለች ባሌ እንደገለፁት፤ ፈተናዉ ወቅታዊ የሆነ አቅማችንን ለማወቅና በቀጣይም ለምናስተምረዉ የትምህርት አይነት ምዘናዉ ጥሩ እንደነበረ ገልጸዋል።

ዘጋቢ: ብርሀኑ ዳሾ – ከአርባምንጭ ጣቢያችን