የንግድ ትርኢትና ባዛሮች ነጋዴዎችንና ሸማቾችን በማቀራረብ ጥራት ያላቸው ምርቶች በተመጣጣኝ ዋጋ እንዲቀርቡ የሚያስችሉ መሆናቸው ተገለፀ
በጉራጌ ዞን በነጋዴ ሴቶች ማህበር አማካኝነት የተዘጋጀ አረፋን በጉራጌ የንግድ ትርኢት ኤግዚቢሽን እና ባዛር እንዲሁም የባህል ፌስቲቫል በወልቂጤ ከተማ እየተካሄደ ነው።
የጉራጌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አማካሪ አቶ ዳርጌ ተክሉ በመክፈቻ ንግግራቸው እንዳሉት፤ ባዛሩ ከሚሰጠው ኢኮኖሚያዊ ጥቅም ባሻገር የህዝብ ለህዝ ግንኙነትን የሚያጠናክር ነው።
የጉራጌ ዞን የነጋዴ ሴቶች አስተባባሪ ወይዘሮ ሮዛ አግዛ አዶት፤ የጉራጌ ነጋዴ ሴቶች ማህበር በ2016 አመተ ምህረት የተቋቋመ ሲሆን በዞኑ ከሚገኙ 8 ሺህ 111 ሴት የነጋዴ ማህበረሰብ ክፍሎችን ያቀፈ ነው ብለዋል።
ማህበሩ በዋናነት አላማ አድርጎ የተነሳው በነጋዴው ማህበረሰብ እና በመንግስት መካከል እንደድልድይ በመሆን ዘርፈ ብዙ ስራዎች እያከናወነ ይገኛልም ሲሉ ተናግረዋል።
መንግስት ለነጋዴ ሴት ማህበራት በአዋጅ ካጎናጸፋቸው መብቶች መካከል አንዱ የንግድ ትርኢት እና ባዛር ማዘጋጀት ነው ያሉት አስተባባሪዋ፤ በዚህም ማህበራቱ የገቢ አቅማቸውን ለማሳደግና የኢኮኖሚ አበርክቷቸውን ለማላቅ እንደሚያስችል አስረድተዋል።
የወልቂጤ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ሙራድ ከድር በበኩላቸው፤ የአረፋ በአልን ምክንያት በማድረግ የንግድ ትርኢትና ባዛር መካሄዱ ሸማቹ ህብረተሰብ ጥራት ያለው ምርት በተመጣጣኝ ዋጋ እንዲያገኝ የሚያስችለው መሆኑን ተናግረዋል።
ከተማዋን እድሜዋን የሚመጥን ወቅቱን የዋጀ ውብና ማራኪ ገጽታ እንድትላበስ ከማድረግ ጎን ለጎን ኢኮኖሚዋን የማነቃቃት ስራ እየተከናወነ ይገኛል ብለዋል።
ከተለያዩ አቅጣጫዎች መጥተው አገልግሎት አየሰጡ የሚገኙ ነጋዴዎች በበአል ወቅት ማህበረሰቡ የሚፈልጋቸውን የፋብሪካ ምርቶች ይዘው መገኘታቸው ፋይዳው የጎላ ሰለመሆኑም አቶ ሙራድ ገልጸዋል።
ከዚህ ባሻገር ለማህበራዊ መስተጋብር መጠናከር አበርክቶው ከፍተኛ መሆኑንም ከንቲባው አስረድተዋል።
የኦሮሚያ ክልል የነጋዴ ሴቶች የወሊሶ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ሃላፊ ወይዘሮ ሙሉ ዋቃዮ፤ የኦሮሞ እና የጉራጌ ህዝቦች የቀደመ ታሪካዊ ግንኙነት እና የእርስ በርስ ትስስር ያላቸው መሆኑን ጠቁመው ዞኑ በክትፎ ብቻ ሳይሆን በእንግዳ ተቀባይነቱም ይታወቃል ሲሉ ተናግረዋል።
በንግድ ትርኢትና ባዛሩ አግኝተን ያነጋገርናቸው ነጋዴዎች በሰጡት አስተያየት ከአረፋ በአልና ከበአሉም ውጪ አገልግሎት ሊሰጡ የሚችሉ የኢንደስትሪ ምርቶች የማህበረሰብን የገቢ አቅም ባገናዘበ እና በተመጣጣኝ ዋጋ እየሸጡ መሆኑን ጠቁመዋል
ዘጋቢ፡ አስቻለው አማረ – ከወልቂጤ ጣቢያችን
More Stories
የኢፌዲሪ ውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር የአፍሪካ ቀንድ ዘላቂ የከርሰ ምድር ውሃ ፕሮጀክት ከ82 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ በማድረግ በጉራጌ ዞን ምሁር አክሊል ወረዳ መቆርቆር ቀበሌ ያስገነባው የንጹህ መጠ ውሃ ፕሮጀክት ተመርቆ ለአገልግሎት ክፍት ሆነ
የኡዱሂያ የዕርድ ስርዓት….የአብሮነት ነፀብራቅ
በቅርቡ በሚሰጠው የ6ኛ እና የ8ኛ ክልላዊ ፈተና ላይ ከ53 ሺህ በላይ ተማሪዎች ለፈተና እንደሚቀርቡ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የሀዲያ ዞን ትምህርት መመሪያ አስታወቀ