ሀዋሳ፡ ግንቦት 20/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) ለተረጋጋ የፖለቲካ ስርዓት እና ባህል ግንባታ የፖለቲካ ፓርቲዎች ሚና ወሳኝ ነው “በሚል መሪ ሀሳብ የጉራጌ ዞን ተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ መድረክ በወልቂጤ ከተማ እየተካሄደ ነው።
በመድረኩ የጉራጌ ዞን የመንግስት ዋና ተጠሪ አቶ አለማየሁ ገ/መስቀል የማዕከላዊ ኢትዮጵያ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክርቤት ሰብሳቢ አቶ ደምስ ገብሬን ጨምሮ ሌሎች የተለያዩ ተፎካካሪ ፓርቲ አመራሮች እና ባለድርሻዎች በመሳተፍ ላይ ናቸው ።
ለአንድ ሀገር የተረጋጋ የፖለቲካ ስርኣትና ባህል ግንባታ ዋናው ተዋኒያን የፖለቲካ ፓርቲዎች ለመሆናቸው ተመላክቷል፡፡
ምርጫ ለሀገር፣ ለትዉልድና ለዲሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ባለዉ ፋይዳ በምርጫ በንቃት መሳተፍ፣ አማራጭ ፖሊሲ ይዞ መቅረብ፣ በሕጋዊ መንገድ በምርጫ መሳተፍ፤ ጥሰቶች ሲያጋጥሙ በመከታተል ሪፖርት ማድግና በጋራ መፍታት፤ የምርጫን ውጤት ለመቀበል መዘጋጀት ለሀገራችን፣ ለህዝብና ለመራጭ ዜጎች ክብር በመስጠት ስልጡን ህዝብና ሀገር መሆናችንን በዓለም ፊት ዳግም የማረጋገጥ ሚና መወጣት ይጠበቃል ፡፡
በ6ኛ ሀገራዊና ክልላዊ ምርጫ እና በቅርቡ በተካሄደዉ በቀሪና የድጋሚ ምርጫ ሂደትና ዉጤት በጋራ በመገምገም ትምህርት በመዉሰድ የምርጫ ወቅት ተግዳሮቶችን ለመፍታትና ለማቃለል የፖለቲካ ፓርቲዎች ሚና የጎላ በመሆኑ ከወዲሁ በጋራ መዘጋጀት ይጠይቃል ተብሏል፡፡
የፖለቲካ ፓርቲዎች እርስ በርስና ከገዢ ፓርቲና ከመንግስት አካላት ጋር የተጀመረዉን ተቀራርቦ የመስራት አዲስ አካሄድ ልምምድን በማጎልበት ወደ ባህል ለማሳደግ ሚናቸዉን እንዲወጡ ሀገራዊና ወቅታዊ መረጃ በመስጠት በትብብር የመስራት ባህል ማጠናከር ያስፈልጋል፡፡
በጋራ መድረኩ የጉራጌ ዞን ብልፅግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ፅህፈት የዴሞክራሲ ባህል ግንባታ ዘርፍ ሀላፊ አቶ ሔኖክ አብዱልሰመድ የውይይት መነሻ ሰነድ አቅርበው ውይይት እየተደረገበት ይገኛል፡፡
ዘጋቢ፡ ሪድዋን ሰፋ – ከወልቂጤ ጣቢያችን

More Stories
በ6 ወራት ውስጥ ሊመዘበር የነበረ ከ156 ሚሊየን 560ሺህ ብር በላይ ማዳን መቻሉ ተገለጸ
የጉራጌ ክትፎ ባህልና እውቀትን በዩኒስኮ የሰው ልጆች ወካይ የማይዳሰስ ቅርስነት ለማስመዝገብ እየተሰራ እንደሚገኝ የኢፌዲሪ ቅርስ ባለስልጣን ገለፀ
በክልሉ ያሉ ብሔረሰቦችን ባህል ወደፊት በማውጣት የአካባቢውን ሰላምና ልማት ለማስቀጠል በትኩረት መስራት እንደሚገባ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ርዕሰ መስተዳደር ኢንጅነር ነጋሽ ዋጌሾ(ዶ/ር) ተናገሩ