ተፎካካሪ የፓለቲካ ፓርቲዎች ለህዝብ ሰላም እና ተጠቃሚነት ተቀራርበው ሊሰሩ እንደሚገባ ተጠቆመ

ተፎካካሪ የፓለቲካ ፓርቲዎች ለህዝብ ሰላም እና ተጠቃሚነት ተቀራርበው ሊሰሩ እንደሚገባ ተጠቆመ

ሀዋሳ፡ ግንቦት 17/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) በጋሞ ዞን የተፎካካሪ የፓለቲካ ፓርቲዎች ለህዝብ ሰላም እና ተጠቃሚነት ተቀራርበው ሊሰሩ እንደሚገባ ተጠቆመ።

‎”ለተረጋጋ የፖለቲካ ስርዓት እና ባህል ግንባታ የፖለቲካ ፓርቲዎች ሚና” በሚል ርእስ የፖለቲካ ፓርቲዎች ዞናዊ የውይይት መድረክ በአርባምንጭ ከተማ ተካሂዷል።

የመድረኩ አላማ ተፎካካሪ የፓለቲካ ፓርቲዎች በተናጠል እና በጋራ ሃገራዊ ለውጡ አሁን የደረሰበትን ደረጃ ተረድተው በቀጣይ አቅጣጫዎች ዙሪያ በመተማመን ተቀራርበው እንዲሰሩ ማስቻል መሆኑ ተመላክቷል።

‎መንግስትን በመወከል በመድረኩ የተገኙት የጋሞ ዞን ህዝብ ምክርቤት ዋና አፈጉባኤ ወ/ሪት አለሚቱ ዮሴፍ በአገሪቱ በ7 አመታት ውስጥ በኢኮኖሚ፣ በፖለቲካ እና በማህበራዊ ዘርፍ የተመዘገበውን ስኬት ተፎካካሪ ፓርቲዎች በውል ተረድተው ጤናማ የሆነ ፉክክር ሊያካሂዱ እንደሚገባ ተናግረዋል።

‎በፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት በቀረበው ሰነድ ሃገራዊ ለውጡን ያጋጠሙ ፖለቲካዊ ተግዳሮቶች በዝርዝር የቀረበ ሲሆን የጽንፈኝነት፤ የፖለቲካ አለመረጋጋት እና ግጭት ከአስተሳሳሪ ትርክት ይልቅ በነጠላ ትርክት ላይ ማተኮር በተግዳሮትነት ተነስቷል።

‎የኢሶዴፓ ፓርቲ ተወካይ አቶ ወንድሙ ኡቶ እንደተናገሩት ተፎካካሪ ፓርቲዎች የሃይል አማራጭ ከመጠቀም ወጥተው ለወከላቸው ህዝብ ተጠቃሚነት አበክረው መስራት አለባቸው።

‎ህብር ኢትዮጵያ ፖርቲን በመወከል የተገኙት አቶ አለማየሁ ገ/መድህን ደግሞ ገዢው መንግስት ከተፎካካሪ ፖርቲዎች ጋር ለመስራት ፍላጎት ማሳየት ያለበት ምርጫ ሲቃረብ ብቻ መሆን እንደሌለበት ጠቁመው፥ የኑሮ ውድነቱን ለማረጋጋት መንግስት በቁርጠኝነት መስራት አለበትም ሲሉ አፅንኦት አሳስበዋል።

‎የመኢኣድ ፓርቲን ወክለው የተገኙት አቶ ወንዱ ወንዳፍራሽ የዞኑ የፖለቲካ ፓርቲ ተወያይቶ በስራ እድል ፈጠራና በኑሮ ውድነት ላይ ለውጥ ማምጣት እንዲችል በጋራ መስራት ይጠበቃል።


ከእናት ፓርቲ የተገኙት የጋሞ ዞን ተፎካካሪ ፓርቲዎች ምክር ቤት ሰብሳቢ አቶ ቴዎድሮስ ፋንታ በውይይት መድረኩ መዘጋጀት የተሰማቸውን አድናቆት ገልጸው በሃገሪቱ አንጻራዊ የፖለቲካ ምህዳር መስፋቱን መስክረዋል።

የእናት ፓርቲ ተወካይ ‎ወ/ሮ የትምወርቅ ነጋሽ በሃገራዊ ለውጡ ዙሪያ የጋራ መግባባት ለመፍጠር የቀረበው ሰነድ ይዘትን አወድሰው ፤ሃገራዊ ሰላምን ለማስጠበቅ ብሎም የኑሮ ውድነትን በመቆጣጠር በኩል መንግስት በትኩረት መስራት ያሻዋል ብለዋል።

ዘጋቢ: አሰግድ ተረፈ – ከአርባ ምንጭ ጣቢያችን