በድንበር ተሻጋሪ ወንዞቻችን የጋራ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ በዲፕሎማሲው ዘርፍ የተጠናከረ ስራ ሊሰራ እንደሚገባ የኢፌዲሪ ውሀና ኢነርጂ ሚኒስቴር አስታወቀ
23ኛው አለም አቀፍ ሲምፖዚየም “የውሀ ሀብት ለዘላቂ ልማትና ተጠቃሚነት” በሚል መሪ ቃል በአርባምንጭ ዩኒቨርሲቲ ተካሂዷል።
በአርባምንጭ ዩኒቨርሲቲ የምርምርና ትብብር ምክትል ፕሬዝዳንት ዶ/ር ተክሉ ወጋየሁ፤ የሲምፖዚየሙ መዘጋጀት የውሀ ሀብትን በዘላቂነት ለመጠቀም እንዲያስችል የዘርፉ ምሁራን ሀሳባቸውን፣ ፈጠራቸውንና ተሞክሯቸውን እንዲያጋሩ ታልሞ የተዘጋጀ መሆኑን ጠቁመዋል።
ለፖሊሲ አውጭዎችና ለሚዲያ ባለሙያዎች ለሀገራችን የውሀ ሀብት አጠቃቀም የሚሻለውን በመለየት መጠቀም የሚያስችል እውቀት የሚያስጨብጥ ነውም ብለዋል።
መሰል ሲምፖዚየሞች ድንበር ተሻጋሪ የሆኑ ወንዞችን ለመጠቀም የሚያስችል የውሀ ዲፕሎማሲያችንን ለማጠናከር ያግዛል ሲሉ ገልጸዋል።
የአርባምንጭ ዩኒቨርሲቲ ውሀ ቴክኖሎጂ ኢንስትትዩት ሳይንቲፊክ ዳይሬክተር ዶ/ር ታምሩ ተሰማ፤ በዩኒቨርሲቲው ለበርካታ አመታት የውሀ ሀብታችንን ለዘላቂ ልማት መጠቀም የሚያስችል ዘርፈ ብዙ ጥናቶች ተጠንተው ውጤት በሚያመጣ መልኩ እየተሰራ ነው፡፡ ለዚህም የዘርፉ ምሁራን ድርሻ የጎላ ነው ብለዋል።
የኢፌዲሪ ውሀና ኢነርጂ ሚኒስቴር ሚኒስትር ልዩ አማካሪ ዶ/ር ሚካኤል መሀሪ፤ ምርምርና የኢንዱስትሪ ስራዎች የሚነጣጠሉ ባለመሆናቸው የአርባምንጭ ዩኒቨርሲቲ በውሀ ሀብት አስተዳደርና ዘላቂ ተጠቃሚነት እንዲሁም በተፋሰስ ስራዎች ላይ እየተሰሩ ያሉ እቅዶችና እየቀረቡ ያሉ ፕሮጀክቶች በይበልጥ ሊተኮርባቸው እንደሚገባ ገልጸዋል።
በተለይ 75 ከመቶ በላይ የሚሆነው የሀገራችን ተፋሰስ ወደ ጎረቤት ሀገራት የሚፈስ በመሆኑና በጋራ የምንጠቀማቸው በመሆኑ በዲፕሎማሲው ረገድ ድንበር ተሻጋሪ ወንዞቻችንን ለመጠቀም በሚያስችለን ጉዳይ መረጃ ለአለም እንዲደርስ ከማድረግ አኳያ እየተሰሩ ያሉ ጥናቶች ተጠናክረው መቀጠል አለባቸው ብለዋል።
ዘጋቢ፡ ማርታ ሙሉጌታ – ከአርባምንጭ ጣቢያችን
በድንበር ተሻጋሪ ወንዞቻችን የጋራ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ በዲፕሎማሲው ዘርፍ የተጠናከረ ስራ ሊሰራ እንደሚገባ የኢፌዲሪ ውሀና ኢነርጂ ሚኒስቴር አስታወቀ

More Stories
የግል እና የጋራ መጸዳጃ ቤቶችን በተገቢው በመጠቀም ተላላፊ የሆኑ በሽታዎችን አስቀድሞ መከላከል እንደሚገባ በጉራጌ ዞን የእኖር ወረዳ ጤና ጥበቃ ጽህፈት ቤት አስገነዘበ
12 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር በተቋማት የድርጊት መርሐ-ግብርና በፀደቀላቸው በጀት መሠረት ማሰራጨቱን የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ፋይናንስ ቢሮ አስታወቀ
የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው(ዶ/ር) በምስራቅ ጉራጌ ዞን ቡኢ ከተማ አስተዳደር እየተገነባ የሚገኘውን ብሉ ኤለፋንት ፋይበር ቦርድ ካምፓኒ ጎበኙ