የጤናው ዘርፍ ተግባራት በኃላፊነት እና በቅንጅት ሊሰራ እንደሚገባ ተገለጸ

‎የጤና ተግባራት በኃላፊነት እና በቅንጅት ሊሰራ እንደሚገባ የይርጋጨፌ ወረዳ ጤና ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ተካልኝ ጥላሁን ገለጹ።

የፒ.ኤስ.አይ ኢትዮጵያ መንግስታዊ ያልሆነ ድርጅት ከይርጋጨፌ ጤና ጥበቃ ጽ/ቤት ጋር በመተባበር “የማህበረሰብ ተሳትፎ ለጤና” በሚል መሪ ሀሳብ ከባለድርሻ አካላት ጋር የውይይት መድረክ አካህዷል።

‎በመድረኩ ተገኝተው መልዕክት ያስተላለፉት የይርጋጨፌ ወረዳ ጤና ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ተካልኝ ጥላሁን፥ የጤና ተግባር ሁሉም ሴክተሮች በኃላፊነት እና በቅንጅት የሚሠሩት ሊሆን እንደሚገባ አሳስበዋል።

እናቶች በጤና ተቋም እንዲወልዱ ከቅድመ ወሊድ ጀምሮ እስከ ድህረ ወሊድ ያለውን ጊዜ ክትትል እንዲያደርጉ በስፋት መሰራት እንዳለበት አቶ ተካልኝ አንስተዋል።

‎አምራች ዜጋን ለማፍራት የህጻናት መቀንጨር ትልቅ ማነቆ መሆኑን የገለፁት ኃላፊው፥ ለብሩህ አእምሮ እና ዕድገት የተመጣጠነ ምግብ ማግኘት አለባቸው ብለዋል።

‎በፒ.ኤስ.አይ ኢትዮጵያ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል አስተባባሪ ዶ/ር ታምራት ተስፋዬ፣ ድርጅቱ በርካታ ስራዎችን ሲሰራ መቆየቱን አንስተው፥ በእናቶች እና ህጻናት ጤና እና በስርዓተ ምግብ ፕሮግራም ለመዘርጋት እና ማስተዋወቂያ የውይይት መድረክ መሆኑን ጠቁመዋል።

‎በወረዳው ለሁለት ዓመታት እንደሚቆይ ያነሱት አስተባባሪው፥ በቆይታ ጊዜያቸውም በስርዓተ ምግብ፣ በእናቶች እና ህጻናት ጤናና ሌሎች የጤና አመለካከቶች ላይ ግንዛቤ የማስጨበጥ ስራ እንደሚሰራ ገልጸዋል።

‎የይርጋጨፌ ወረዳ ምክትል አስተዳዳሪ አቶ ተካልኝ በቀለ በበኩላቸው፣ የማህበረሰብ ጤና ልማትን ለማረጋገጥ ዘርፈ ብዙ ተግባራት እየተሰሩ መሆናቸውን ገልጸው፥ ድርጅቱ የማህበረሰቡን የጤና ችግር ለመቅረፍ ላደረገው አስተዋጽኦ አመስግነዋል።

‎አስተያየታቸውን የሰጡ የውይይቱ ተሳታፊዎች በበኩላቸው፥ ዉይይቱ አስፈላጊ መሆኑን በመግለጽ የህብረተሰቡን ጤና ለመጠበቅ በቅንጅት እንደሚሰሩ ተናግረዋል።

‎ዘጋቢ፡ አሀዱ አሸናፊ – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን