ባለፉት አመታት የመሬት አስተዳደርና አጠቃቀም ስርአትን በማዘመን የተሰሩ ስራዎች አርሶ አደሩን ተጠቃሚ ማድረጋቸውን የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ግብርና ቢሮ የመሬት አስተዳደርና አጠቃቀም ኤጀንሲ አስታወቀ

ባለፉት አመታት የመሬት አስተዳደርና አጠቃቀም ስርአትን በማዘመን የተሰሩ ስራዎች አርሶ አደሩን ተጠቃሚ ማድረጋቸውን የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ግብርና ቢሮ የመሬት አስተዳደርና አጠቃቀም ኤጀንሲ አስታወቀ

ቢሮው ዲጂታል የመሬት መረጃ ስርአት ግንባታ ለፍትሐዊ አስተዳደርና ለተፋጠነ ልማት በሚል መሪ ቃል የ2018 በጀት አመት አፈፃፀም የ2019 ዕቅድና የCalm-1 መዝጊያ ፕሮግራም ላይ ከባለድርሻ አካላት ጋር በሀላባ ቁሊቶ ከተማ ወይይት አካሂዷል።

በወይይት መድረኩ በመገኘት የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ግብርና ቢሮ ኃላፊ ተወካይና የጽህፈት ቤቱ ኃላፊ አቶ አህመድ ሀቢብ፤ ባለፉት አመታት በክልሉ የመሬት አስተዳደርና አጠቃቀም ስርአትን ለማዘመን በተደረጉ ጥረቶች ውጤት ማምጣት መቻሉን ገልፀዋል።

ከዚህ ቀደም የነበረው ባህላዊ የመሬት አያያዝ ስርአት አርሶአደሩን ለወሰን ግጭትና ለመልካም አስተዳደር ችግሮች ያጋልጥ እንደነበር ያስታወሱት ኃላፊው፤ ዘመናዊ የመሬት መረጃ ስርአቱ የገጠር መሬት አጠቃቀምን ውጤታማ እንዳደረገው ገልፀዋል።

የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ግብርና ቢሮ የመሬት አስተዳደርና አጠቃቀም ኤጀንሲ ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ አብድላሀፊዝ ሁሴን በበኩላቸው፤ ባለፉት አመታት በክልሉ በገጠር መሬት የተመዘገቡ ስኬቶች መነሻቸው የመሬት አስተዳደርን በዲጂታል ቴክኖሎጂ በማዘመን አጥጋቢ የመረጃ ስርአት መገንባት መቻሉ እንደሆነ ገልፀዋል።

በክልሉ በርካታ ሴቶች፣ አካል ጉዳተኞች፣ ህፃናትና አርሶአደሩ የመሬት ይዞታቸውን በዲጂታል ስርአት በመመዝገቡ ሙሉ የይዞታ ዋስትና ማግኘታቸውን የገለፁት ዋና ስራ አስኪያጁ፤ ይህም በመሬት ላይ መዋዕለ ንዋያቸውን እንዲያፈሱ በማድረግ የክልሉን ምርትና ምርታማነት እንዲጨምር አድርጓል ብለዋል።

ዘጋቢ፡ ቴዎድሮስ ወርቅነህ