መምህር ትውልድ በመቅረፅና በመገንባት ለሀገር እድገትና ብልጽግና ትልቅ አስተዋጽኦ እንዳለው ተገለፀ
በጂንካ ዩኒቨርሲቲ “ትውልድ በመምህር ይቀረፃል፤ ሀገር በትምህርት ትበለፅጋለች” በሚል መሪ ቃል ከአጠቃላይ መምህራን ጋር የውይይት መድረክ ተካሂዷል።
የጂንካ ዩኒቨርሲቲ ተጠባባቂ ፕሬዚዳንት ዶክተር ዮሐንስ ይትባረክ፤ መምህር ትውልድ በመቅረፅና በመገንባት ለሀገር እድገትና ብልጽግና ትልቅ አስተዋጽኦ እንዳለው ገልፀው በመማር ማስተማር፣ በምርምር፣ በማህበረሰብ አገልግሎት እንዲሁም በቴክኖሎጂ ሽግግር ካላቸው አበርክቶ አንፃር መምህራን በእውቀትና በክህሎት እራሳቸውን ማሳደግ አለባቸው ብለዋል።
የኣሪ ዞን ዋና አስተዳዳሪና የጂንካ ዩኒቨርሲቲ የስራ አመራር ቦርድ አባል አቶ አብርሃም አታ በበኩላቸው፤ መምህራን ለሀገር ግንባታ ያላቸው ሚና ከፍተኛ በመሆኑ ሚናቸውን አጠናክረው እንዲቀጥሉ በመንግሥት በኩል ተወስደው መሰራት በሚገባቸው ጉዳዮች ላይ በግልፅ ውይይት የተደረገበት መድረክ በመሆኑ ለሰላም ግንባታም ከፍተኛ ሚና እንዳለው ገልፀዋል።
በሀገራዊ መድረኩ የተገኙት በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የፋይናንስ ቢሮ ሃላፊ አቶ ተፈሪ አባተ፤ ለተያዘው ለብልጽግና ጉዞ መምህራን ጉልህ ሚና እንዳላቸው ገልፀው በተለይ የዩኒቨርሲቲ መምህራን የሚያስተምሯቸው ተማሪዎች በኢኮኖሚያዊ፣ ፖለቲካዊና ማህበራዊ ጉዳዮች ላይ ስለሚሳተፉ የትምህርት ስብራትን በመጠገን ጥራቱ ላይ ለዉጥ በሚያመጡ ጉዳዮች ላይ መንግስት ከፍተኛ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ ነው ብለዋል።
የውይይቱ ተሳታፊ መምህራን በሰጡት አስተያየት መንግስት በትምህርትም ሆነ በሌሎች ዘርፎች የሚሰራቸው ስራዎች የሚበረታቱ ናቸው ብለው የትምህርት ስብራትን ለመጠገን ከመንግስት ጎን በመሆን ሃላፊነታቸውን እንደሚወጡና መንግስትም የሚነሱ ችግሮችን ትኩረት ሰጥቶ መፍታት እንደአለበት አንስተዋል።
ዘጋቢ፡ ዳኛቸው ደሴ – ከጂንካ ጣቢያችን
More Stories
የኢፌዲሪ ውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር የአፍሪካ ቀንድ ዘላቂ የከርሰ ምድር ውሃ ፕሮጀክት ከ82 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ በማድረግ በጉራጌ ዞን ምሁር አክሊል ወረዳ መቆርቆር ቀበሌ ያስገነባው የንጹህ መጠ ውሃ ፕሮጀክት ተመርቆ ለአገልግሎት ክፍት ሆነ
የኡዱሂያ የዕርድ ስርዓት….የአብሮነት ነፀብራቅ
በቅርቡ በሚሰጠው የ6ኛ እና የ8ኛ ክልላዊ ፈተና ላይ ከ53 ሺህ በላይ ተማሪዎች ለፈተና እንደሚቀርቡ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የሀዲያ ዞን ትምህርት መመሪያ አስታወቀ