ሀዋሳ፣ ግንቦት 15/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) በቦንጋ ዩኒቨርሲቲ “ትውልድ በመምህር ይቀረጻል ፤ ሀገር በትምህርት ይበለጽጋል” በሚል መሪ ቃል የመምህራን ውይይት እየተካሄደ ነው።
የዩኒቨርሲቲው ተጠባባቂ ፕሬዝደንት ዶክተር ደገለ ኤርገኖ፤ የመድረኩ ዓላማ የመምህራንን ሀሳብ ለማድመጥና እርስ በእርስ መወያየት የሚችሉበትን ሁኔታ መፍጠር ነው ብለዋል።
መንግስት ለሚሰራቸው ስራዎች ግብዓት የሚሆኑ ሀሳቦችን ከምሁራን ለማግኘትና ተግባራዊ ለማድረግ በሀገር-አቀፍ ደረጃ ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ጋር ውይይት እየተደረገ መሆኑን ጠቁመዋል።
የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ምክትል ርዕሰመስተዳድርና የግብርና ቢሮ ኃላፊ አቶ ማስረሻ በላቸው፤ መምህርነት ለሀገር ጠቃሚ ዜጎችን የሚያፈሩበት የተከበረ ሙያ ነው ብለዋል።
ሀገራዊ ለውጡ አሁን የደረሰበትን ደረጃና ቀጣይ አቅጣጫዎችን በሚመለከት ባቀረቡት የመወያያ ሰነድ አሰባሳቢ ትርክትን ለመፍጠርና ህብረ-ብሔራዊነትን ለማፅናት የመምህራን አስተዋፅኦ ከፍተኛ ነው ብለዋል።
የትምህርት ዘርፍ ሙያዊ ነፃነቱ ተጠብቆ እንዲቀጥልና ሀገርን መምራት የሚችሉ ምሁራንን ለማፍራት እንዲቻል በመንግስት ደረጃ ትኩረት ተሰጥቶ መሰራቱን ነው የተናገሩት።
በትምሀርት ዘርፍ ከተከናወኑ የለውጥ ስራዎች መካከል ሙያዊ ነፃነትን ለማስከበር፣ የፈተና አሰጣጥንና አጠቃላይ የትምህርት ስርዓቱን ለማሻሻል መሰራቱን ጠቅሰዋል።
በዚህም የትምህርት ጥራትን በማረጋገጥ ተጨባጭ ለውጥ መታየት ጀምሯል ነው ያሉት።
የተወዘፉ የትምህርት ዘርፍ ችግሮችን በመለየት ባለፉት ሰባት ዓመታት ለውጥ መታየቱን ገልፀዋል።
በመድረኩ ሀገራዊ ነባራዊ ሁኔታዎችን እና የቀጣይ ስራ አቅጣጫዎችን የሚመለከት ሰነድ ቀርቦ ውይይት እየተደረገበት ይገኛል።
ዘጋቢ፡ ዮሐንስ ክፍሌ – ከቦንጋ ጣቢያችን

More Stories
የፀረ-ተህዋስያን መድኃኒቶች በጀርሞች መላመድን ለመከላከል በሚደረገው አገራዊ ጥረት ውስጥ የሚዲያ ባለሙያዎች ግንባር ቀደም ሚና ሊጫወቱ እንደሚገባ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ ገለጸ
መምህራን የሚገባቸውን ጥቅማ ጥቅምና መብት በማስጠበቅ የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ በትኩረት እየተሰራ እንደሚገኝ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል መምህራን ማህበር አስታወቀ
የልማትና መልካም አስተዳደር ተግባራትን ለማፋጠን ግብር ከፋዩ የሚጠበቅበትን ታክስ በወቅቱና በታማኝነት መክፈል እንዳለበት ተገለጸ