በወላይታ ዞን ዳሞት ወይዴ ወረዳ በጤና አገልግሎት አሰጣጥ ዙሪያ ከጤና ባለሙያዎች ጋር የምክክር መድረክ ተካሂዷል

በወላይታ ዞን ዳሞት ወይዴ ወረዳ በጤና አገልግሎት አሰጣጥ ዙሪያ ከጤና ባለሙያዎች ጋር የምክክር መድረክ ተካሂዷል

ህብረተሰቡ የተሻለ የህክምና አገልግሎት እንዲያገኝ መንግስት ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑም ተገልጿል።

አቶ ዝግጁ ሎሪሶ እና ሲስተር ካሰች አለማየሁ በመድረኩ የተገኙ የጤና ባለሙያዎች ሲሆኑ በአሁን ወቅት ለጤና ሥራ ማነቆ እየሆኑ ያሉ ችግሮችን ገልፀው ለችግሮቹ አፋጣኝ ምላሽ እንዲሰጥ ጠይቀዋል።

በጤናው ዘርፍ ህብረተሰቡ የሚፈልገውን አገልግሎት በቅንነት መስጠት ላስተማረው ቤተሰብ እና ለሀገሪቱ የሚሰጥ ክብር መሆኑ ተገልጿል።

የጤና ባለሙያዎች በርካታ ጥያቄዎችን ለመንግሥት እያቀረቡ ያሉበት ወቅት መሆኑን የገለፁት ከጤና ባለሙያዎች መካከል አቶ ክፍሌ ለማ እና አቶ መንግሥቱ ቢንቤሶ በበኩላቸው፤ ለጥያቄያቸው መንግስት አስፈላጊ ምላሽ እስኪሰጥ ድረስ አስፈላጊ አገልግሎት ለህብረተሰቡ እየሰጡ እንደሚቀጥሉ ተናግረዋል።

አክለውም የጤና ባለሙያዎችን ጥያቄ ምክንያት በማድረግ በመንግሥትና በህዝብ መካከል ችግር ለመፍጠር የሚሹ አካላት ከድርጊታቸዉ እንዲቆጠቡም የጤና ባለሙያዎቹ አሳስበዋል።

የጤና ባለሙያዎች ለህብረተሰቡ ያለስስት አገልግሎት ሲሰጡ በመቆየታቸው ሊመሰገኑ ይገባል ያሉት የዳሞት ወይዴ ወረዳ ጤና ጥበቃ ጽህፈት ቤት ኃላፊ ወ/ሮ ሰላማዊት መኮንን፤ በቀጣይም ለህብረተሰቡ የተሳለጠ አገልግሎትን ተደራሽ ለማድረግ በትኩረት እንሰራለን ብለዋል።

ለህብረተሰቡየተሻለ አገልግሎት ለመስጠት የተደረገ መድረክ መሆኑንም ወ/ሮ ሰላማዊት ገልጸዋል።

በመድረኩ የተገኙት የወላይታ ዞን የመንግስት ዋና ተጠሪ አቶ ዘዉዱ ሳሙኤል በበኩላቸው፤ ህብረተሰቡ የተሻለ የህክምና አገልግሎት እንዲያገኝ መንግስት ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ ይገኛል ብለዋል።

ለጤና ባለሙያዎች ጥያቄም ዘላቂ መፍትሔ ለመስጠት በትኩረት እየተሠራ መሆኑንም አቶ ዘዉዱ ጠቁመዋል።

ዘጋቢ፡ ሰላሙ መሴቦ – ከዋካ ጣቢያችን