የበልግ አዝመራ ከ9 ነጥብ 5 ሚሊየን በላይ የእንሰት ችግኝ መተከሉ ተገለጸ

ሀዋሳ፡ ግንቦት 12/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) በተገባደደዉ የበልግ አዝመራ ከ9 ነጥብ 5 ሚሊዮን በላይ የእንሰት ችግኝ መተከሉን በሸካ ዞን የአንድራቻ ወረዳ እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ፅ/ቤት አስታውቋል።

ወረዳው ምርትና ምርታማነት በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በትኩረት እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል።

በበልግ አዝመራ በእንሰት፣ በቦቆሎ፣ በድንች፣ በአትክልትና ፍራፍሬ እንዲሁም በቦሎቄ ከ8 ሺህ 656 ሄክታር በላይ መሬት በዘር ለመሸፈን ታቅዶ 6ሺህ 932 ሄክታር መሸፈን መቻሉን የአንድራቻ ወረዳ እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ፅ/ቤት ኃላፊ አቶ አክሊሉ ሸነኖ አስታዉቋል።

ወረዳዉ ለእንሰት ተክል በሰጠው ትኩረት በ3 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ 12 ሚሊየን የእንሰት ችግኝ ለመትከል አቅዶ በ2 ሺህ 687 ሄክታር መሬት ላይ በተለያዩ ደረጃ የሚገኙ 9 ነጥብ 5 ሚሊየን የእንሰት ችግኝ መተከሉንም ገልፀዋል።

በበልግ አዝመራ የተተከሉትና የተዘሩ ሰብሎች ውጤታማ ለማድረግ አርሶ አደሩ የአረም ሳምንታትን ተከታትሎ በመቆጣጠርና በመንከባከብ ተጠቃሚነቱን ማረጋገጥ እንደሚገባም ጠቁመዋል ።

ዘጋቢ: ግርማ ጮሪቶ – ከማሻ ጣቢያችን