የፍትህ ስርዓቱን ዘመናዊ፣ ተደራሽ፣ ቀልጣፋና ውጤታማ ለማድረግ እየተሰራ እንደሚገኝ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልላዊ መንግስት የፍትህና ህግ ኢንስቲትዩት አስታወቀ

‎በጋብቻ፣ ፍቺና ንብረት ክፍፍል የህግ ማዕቀፎች እና አተገባበር ዙሪያ ከክልሉ ፍርድ ቤቶች ለተውጣጡ ዳኞች ስልጠና በአርባምንጭ ከተማ እየተሰጠ ይገኛል።

‎የክልሉን ህዝብ የፍትህ ጥማት ለማርካትና ተገቢውን አገልግሎት ለመስጠት በተለይም በፍትህ ተቋማት የሚታዩ የክህሎት፣ የስነ-ምግባርና የአሰራር ክፍተቶችን ለማረም የደቡብ ኢትዮጵያ ክልላዊ መንግስት የፍትህና የህግ ኢንስቲትዩት በአዋጅ ቁጥር 13/2016 ተቋቁሞ ወደስራ ገብቷል።

‎በዚህም የፍትህ ስርዓቱን ዘመናዊ፣ ተደራሽ፣ ቀልጣፋና ውጤታማ ለማድረግ የሚረዱ የህግ ጥናትና ምርምሮችን እያካሄደ እንደሚገኝ የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር አቶ ካሳሁን ፍልፍሉ በእንኳን ደህና መጣችሁ ንግግራቸው ገልፀዋል።

‎አክለውም “ፍትህ በገንዘብ ይሸጣል” የሚለው ወቀሳና ትችት የፍትህ ባለሙያዎች ሁሉም የክህሎት፣ የአመለካከት እና የስነ-ምግባር ችግር ስላለበት ሳይሆን እንደባለሙያዎቹ ባህሪ እና አቅም ሁኔታ የሚንፀባረቁ ችግሮች መሆናቸውን ገልፀው የሚታዩ ችግሮችን ታግለን በማረም የተቋማችንን ክብር መጠበቅ የሁላችንም ኃላፊነት ሊሆን ይገባል ብለዋል።

‎የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዚዳንትና የፍትህ እና ህግ ኢንስቲትዩት ስራ አመራር ቦርድ ሰብሳቢ አቶ ቦጋለ ፈይሳ በመክፈቻ ንግግራቸው እንዳሉት፤ በጋብቻ፣ ፍቺና የንብረት ክፍፍል ዙሪያ ዳኞች በትኩረት መስራት አለባቸው።

‎ቤተሰብ የህብረተሰብ መሰረት፣ ህብረተሰብ ደግሞ የሀገር መሰረት መሆኑን ያወሱት አቶ ቦጋለ፤ ሀገርን ለመጠበቅ ሲባል ለቤተሰብ ህጉ ብርቱ ጥንቃቄ ማድረግ ከዳኝነት አካሉ እንደሚጠበቅ ገልጸው ስልጠናውን ወደ ተግባር መቀየር ይጠበቅብናል ሲሉ አሳስበዋል።

‎በጋብቻ፣ ፍቺና ንብረት ክፍፍል የህግ ማዕቀፎች እና አተገባበር ዙሪያ ከክልሉ ፍርድ ቤቶች ለተውጣጡ ዳኞች ስልጠና እየተሰጠ ይገኛል።

‎ዘጋቢ፡ ተመኙህ ገረሱ – ከአርባምንጭ ጣቢያችን‎