ሀዋሳ፡ ግንቦት 08/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) የባህል ፀጋዎቻችንን በአግባቡ መጠቀምና ማስተዋወቅ የአብሮነትን መሰረት እንደሚያጠናክር የኢፌዲሪ ባህልና ስፖርት ሚኒስቴር አስታውቋል፡፡
ሚኒስቴሩ ከደቡብ ኢትዮጵያ ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ጋር በመተባበር በአርባ ምንጭ ከተማ “ባህላዊ ሀብቶችን ለአብሮነት መጠቀም” በሚል ርዕስ ሲምፖዚየም እያካሄደ ይገኛል።
ሲምፖዚየሙ በሀገር ሽማግሌዎች የምርቃት ሥነ-ሥርዓት እና በጋሞ ዞን አስተዳደር የእንኳን ደህና መጣችሁ መልዕክት ተጀምሯል።
የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የኢፌዲሪ ባህልና ስፖርት ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ ወ/ሮ ነፊሳ አልማህዲ፤ “ሀገራችን የበርካታ ብሔሮችና ብሔረሰቦች መገኛ ናት፤ ትውልዶች በአንድነት ሀገራቸውን ጠብቀው አስቀጥለዋል። ዛሬም ይህንኑ አንድነትና መተባበርን አጠናክረን መቀጠል እንችላለን” ብለዋል።
”የኢፌዲሪ ህገ መንግሥትም ይህንን መርህ በግልጽ አስቀምጧል” ያሉት ሚኒስትሯ የባህል ዘርፍ ሀገራዊ አንድነትን፣ ወዳጅነትንና ወንድማማችነትን በማጠናከር ለትውልድ እንዲተላለፍ መንግሥት ልዩ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል።
በተለይም የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በባህላዊ ትስስር የበለጸገ በመሆኑ ይህንኑ መልካም አጋጣሚ ይበልጥ ለማጠናከር ይህ ሲምፖዚየም እንደተዘጋጀ ተናግረዋል።
በመድረኩ ላይ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ኃላፊ ወ/ሮ ወይንቱ መልኩ በበኩላቸው፤ “ሀገራችን የብዙ ብሔሮችና ብሄረሰቦች መኖሪያ ናት፤ የጋራ ደም፣ ረጅም ታሪክና የቋንቋ ትስስርም አለን” ብለዋል።
ክልሉ የ32 ብሄሮችና ብሔረሰቦች መኖሪያ ሲሆን እነዚህ ብሄሮችና ብሔረሰቦች ከጥንት ጀምሮ በአንድነትና በመቻቻል እዚህ መድረሳቸውን ጠቅሰዋል።
ይህንን መልካም አብሮነት የበለጠ ማዳበር የሁላችንም ኃላፊነት መሆኑን ያሳሰቡት ኃላፊዋ፤ መንግሥትም ይህንኑ ለማረጋገጥ የተለያዩ ሥራዎችን እያከናወነ እንደሚገኝ ተናግረዋል።
ባህላዊ እሴቶቻችንን የማልማትና የማስተዋወቅ ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የገለጹ ሲሆን ይህ ሲምፖዚየምም የብሔረሰቦችን ወዳጅነት ለማጠናከርና አብሮነታችንን ለማሳደግ ያለመ መሆኑን አስረድተዋል።
ለዚህ ሲምፖዚየም የውይይት መነሻ እንዲሆኑ የደቡብ ኦሞ፣ የኮንሶ እና የሀገር ሽማግሌዎች ፎረም ያዘጋጇቸው ሰነዶች ቀርበዋል።
ዘጋቢ፡ አማሮ አርሳባ – ከአርባምንጭ ጣቢያችን
More Stories
ከአረንጓዴ አሻራ ችግኝ ተከላ ባሻገር ባህርዛፍን ከእርሻ ቦታ በማንሳት በሌሎች ተክል የመቀየሩ ተግባራት ተጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባ ተገለጸ
በክልሉ እየተካሄደ ያለው የምግብ ስርዓት ማጠናከሪያ ፕሮግራም ምርትና ምርታማነትን ከማሻሻልም ባለፈ የገበያ ትስስርን በማጠናከር ረገድ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለው ተገለፀ
በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በቀቤና ልዩ ወረዳ በተያዘው የበልግ ምርት ወቅት ከ12 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች በዘር ለመሸፈን ታቅዶ እየተሰራ መሆኑን የልዩ ወረዳው ግብርና ጽህፈት ቤት አስታወቀ