የጎፋ ዞን ሕዝብ ምክር ቤት 4ኛ ዙር መርሃ-ግብር 12ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 10ኛ መደበኛ ጉባኤውን እያካሄደ ይገኛል

የዞኑ ሕዝብ ምክር ቤት ዋና አፈጉባኤ  ወ/ሮ ሀብታምነሽ ግራዝማች ባደረጉት የመግቢያ ንግግር፤ ምክር ቤቶች በሕገ-መንግስት የተሰጣቸውን ሥልጣን ተግባር እየፈፀሙ የዞኑ ሕዝብ ኢኮኖሚያዊ፣ ማኅበራዊና ፖለቲካዊ ጉዞ እንዲፈጥን እንዲሁም የሕዝብን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ መሆናቸውን አብራርተዋል።

የምክር ቤቱ አባላት  ያለፈውን 6ኛ አስቸኳይ ረቂቅ ቃለ ጉባኤ መርምረው አጽድቀዋል።

የምክር ቤቱ የ9 ወራት የሥራ ሪፖርት በዝርዝር ለአባላቱ የቀረበ ሲሆን የዞን፣የወረዳ፣የከተማና የቀበሌያት ምክር ቤቶች የመደበኛ ጉባኤ አፈጻጸም ያለበት ደረጃ በጠንካራ ጎን ተገምግሟል።

የቋሚ ኮሚቴዎች ድጋፍና ክትትል በተመሣሣይ በጠንካራ ጎን ቢገለፅም በዞኑ በተለያዩ ዘርፎች የሚገኘውን አጠቃላይ የጥሬ ገንዘብ ዕዳ ከማስመለስ ረገድ ሰፊ ስራ የሚጠበቅበት መሆኑ ተመላክቷል።

ከኦዲት ግኝት ከማስመለስ  አንጻር የታየው ደካማ አፈጻጸም በአስቸካይ ሊታረም እንደሚገባው በምክር ቤቱ አባላት አስተያየት ተሰጥቶበታል።

የጎፋ ዞን አስተዳደር ምክር ቤት የ9 ወራት ሪፖርት በዞኑ ዋና አስተዳዳሪ ኢንጂነር ዳግማዊ አየለ ቀርቧል፡፡

ምክር ቤት ለሁለት ተከታታይ ቀናት በሚኖረው ቆይታ ልዩ ልዩ ሹመቶችን ምርምሮ እንደሚያጸድቅ ይጠበቃል፡፡

ዘጋቢ: አወል ከድር – ከሳውላ ጣቢያችን