ወቅቱ ከፍተኛ የወባ ወረርሽኝ የሚከሰትበት በመሆኑ ህብረተሰቡ ከመቼውም ጊዜ በላይ የመከላከያ መንገዶችን በመተግበር አስፈላጊውን ጥንቃቄ ሊያደርግ እንደሚገባ ተጠቆመ
በዳውሮ ዞን የከጪ ወረዳ ጤና ጥበቃ ጽ/ቤት የወባ በሽታ መስፋፋትን ለመከላከል ትኩረት ተሰጥቶ እየሰራ መሆኑን ገልጿል።
በአካባቢያቸው የወባ በሽታ ስርጭትን ለመቀነስ በተካሔዱ ተግባራት ስርጭቱን ለመቀነስ ተችሎ የነበረ ቢሆንም መልሶ የማገርሽት ሁኔታ እየታየ መሆኑን ጤና አጠባበቅ ጣቢያ አግኝተን ካነጋገርናቸው ታካሚዎች መካከል አስር አለቃ ተስፋዬ አግዜ፣ አንዳርጌ ሀብቴ እና ወ/ሮ አየለች ተናግረዋል፡፡
እንደ ነዋሪዎቹ ገለፃ በአሁኑ ሰዓት በበሽታው የመያዙ ሁኔታዎች እየሰፋ ቢሆንም አልፎ አልፎ የሚስተዋሉ የመድኃኒት እጥረቶች ተቀርፎ ለበሽታ መከላከል ስራዎቹ በቂ ትኩረት እንዲሰጥ ጠይቀዋል።
የከጪ ጤና አጠባበቅ ጣቢያ ኃላፊ አቶ ቴዎድሮስ ኮቾ በበኩላቸው፤ ወቅቱ ከፍተኛ የወባ ወረርሽኝ የሚከሰትበት በመሆኑ ህብረተሰቡ ከመቼውም ጊዜ በላይ የመከላከያ መንገዶችን በመተግበር አስፈላጊውን ጥንቃቄ በማድረግ ራሱን ሊጠብቅ እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡
አክለውም የበሽታውን መስፋፋትና ስርጭትን ለመከላከል እና ለመቆጣጠር ከሚመለከታቸው ከባለድርሻ አካላት ጋር በመሆን በርካታ ሰራዎችን በመስራት ላይ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡
በባለፉት ወራቶች የወባ በሽታ መከላከል እና መቆጣጠር ስራ ላይ ጥሩ ለውጦች ቢታዩም ከየካቲት ወር ወዲህ ባሉት ወራቶች ውስጥ የመስፋፋቱ ሁኔታ እየጨመረ መምጣቱን በከጪ ወረዳ የጤና ጥበቃ ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ብዙአየሁ ዘርሁን ገልጸዋል።
በወረዳው ሁለት ጤና ጣቢያዎች ብቻ መኖሩ እና የባለሙያ እጥረት መኖሩ እንዲሁም የመድኃኒት ስርጭት በወቅቱ ለማድረግ የአቅርቦት ችግሮች ይበልጥ የወባ በሽታ መከላከል እና መቆጣጠር ስራ እንዳይሰራ ማነቆዎች መሆናቸውንም ጠቁመዋል።
በቀጣይ እነዚህን ችግሮች ለመፍታትና የበሽታውን መስፋፋትን ለመከላከል ከባለድርሻ አካላት ጋር በመሆን እየተሰራ መሆኑን አንስተዋል።
ዘጋቢ፡ አፈወርቅ ኦሹ – ከዋካ ጣቢያችን

More Stories
በክራምት ወራት ሲከውኑት የነበረውን የበጎ ተግባር በበጋ ወራት አጠናክረው እንደሚቀጥሉ በስልጤ ዞን የሁልባረግ ወረዳ በጎ ፍቃደኛ ወጣቶች ተናገሩ
ጥራት ያለውን ትምህርት ለዜጎች ለማድረስ እየተጉ ያሉትን ባለድርሻዎች ማበረታታት የትምህርት ስብራትን ለመጠገን ፋይዳው የጎላ መሆኑን የጌዴኦ ዞን ትምህርት መምሪያ ገለፀ
በሀገር በቀል ዕውቀት የሚታወቀውን የአካባቢውን እምቅ አቅም አጉልቶ በማሳየት የሀገር በቀል ኢኮኖሚ ዕድገት ማፋጠን እንደሚገባ ተገለፀ