ወቅቱ ከፍተኛ የወባ ወረርሽኝ የሚከሰትበት በመሆኑ ህብረተሰቡ ከመቼውም ጊዜ በላይ የመከላከያ መንገዶችን በመተግበር አስፈላጊውን ጥንቃቄ ሊያደርግ እንደሚገባ ተጠቆመ
በዳውሮ ዞን የከጪ ወረዳ ጤና ጥበቃ ጽ/ቤት የወባ በሽታ መስፋፋትን ለመከላከል ትኩረት ተሰጥቶ እየሰራ መሆኑን ገልጿል።
በአካባቢያቸው የወባ በሽታ ስርጭትን ለመቀነስ በተካሔዱ ተግባራት ስርጭቱን ለመቀነስ ተችሎ የነበረ ቢሆንም መልሶ የማገርሽት ሁኔታ እየታየ መሆኑን ጤና አጠባበቅ ጣቢያ አግኝተን ካነጋገርናቸው ታካሚዎች መካከል አስር አለቃ ተስፋዬ አግዜ፣ አንዳርጌ ሀብቴ እና ወ/ሮ አየለች ተናግረዋል፡፡
እንደ ነዋሪዎቹ ገለፃ በአሁኑ ሰዓት በበሽታው የመያዙ ሁኔታዎች እየሰፋ ቢሆንም አልፎ አልፎ የሚስተዋሉ የመድኃኒት እጥረቶች ተቀርፎ ለበሽታ መከላከል ስራዎቹ በቂ ትኩረት እንዲሰጥ ጠይቀዋል።
የከጪ ጤና አጠባበቅ ጣቢያ ኃላፊ አቶ ቴዎድሮስ ኮቾ በበኩላቸው፤ ወቅቱ ከፍተኛ የወባ ወረርሽኝ የሚከሰትበት በመሆኑ ህብረተሰቡ ከመቼውም ጊዜ በላይ የመከላከያ መንገዶችን በመተግበር አስፈላጊውን ጥንቃቄ በማድረግ ራሱን ሊጠብቅ እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡
አክለውም የበሽታውን መስፋፋትና ስርጭትን ለመከላከል እና ለመቆጣጠር ከሚመለከታቸው ከባለድርሻ አካላት ጋር በመሆን በርካታ ሰራዎችን በመስራት ላይ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡
በባለፉት ወራቶች የወባ በሽታ መከላከል እና መቆጣጠር ስራ ላይ ጥሩ ለውጦች ቢታዩም ከየካቲት ወር ወዲህ ባሉት ወራቶች ውስጥ የመስፋፋቱ ሁኔታ እየጨመረ መምጣቱን በከጪ ወረዳ የጤና ጥበቃ ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ብዙአየሁ ዘርሁን ገልጸዋል።
በወረዳው ሁለት ጤና ጣቢያዎች ብቻ መኖሩ እና የባለሙያ እጥረት መኖሩ እንዲሁም የመድኃኒት ስርጭት በወቅቱ ለማድረግ የአቅርቦት ችግሮች ይበልጥ የወባ በሽታ መከላከል እና መቆጣጠር ስራ እንዳይሰራ ማነቆዎች መሆናቸውንም ጠቁመዋል።
በቀጣይ እነዚህን ችግሮች ለመፍታትና የበሽታውን መስፋፋትን ለመከላከል ከባለድርሻ አካላት ጋር በመሆን እየተሰራ መሆኑን አንስተዋል።
ዘጋቢ፡ አፈወርቅ ኦሹ – ከዋካ ጣቢያችን

More Stories
በክልሉ የሚገኙ ነዋሪዎችን ሁለንተናዊ የልማት ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ የሚያስችል ሥራ በትኩረት እየተሠራ እንደሚገኝ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ርዕሰ መስተዳድር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ(ዶ/ር) ገለጹ
የእናቶችንና ጨቅላ ህፃናትን ሞት ለመቀነስ በሚደረጉ ጥረቶች ሁሉም የድርሻውን ሊወጣ እንደሚገባ ተገለፀ
የማእከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርእሰ መስተዳደር (ዶ/ር ) እንዳሻው ጣሰው በተገኙበት በጉራጌ ዞን ወልቂጤ ከተማ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች ምርቃትና የመሰረተ ድንጋይ የማስቀመጥ ስነ-ስረዓት እየተካሄደ ይገኛል