የጂንካ ዩኒቨርሲቲ ከሠራተኞቹ ለታላቁ የህዳሰ ግድብ ግንባታ ማጠናቀቂያ ከ1 ነጥብ 5 ሚሊዮን ብር በላይ ገንዘብ አሰባሰበ

የጂንካ ዩኒቨርሲቲ ከሠራተኞቹ ለታላቁ የህዳሰ ግድብ ግንባታ ማጠናቀቂያ ከ1 ነጥብ 5 ሚሊዮን ብር በላይ ገንዘብ አሰባሰበ

ሀዋሳ፡ ሚያዝያ 25/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) የጂንካ ዩኒቨርሲቲ ከሠራተኞቹ ለታላቁ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ከ1 ነጥብ 5 ሚሊዮን ብር በላይ በቦንድ ግዢ ማሰባሰቡን አስታወቀ።

በዩኒቨርሲቲው መምህራንና የአስተዳደር ሰራተኞች ለታላቁ የህዳሴ ግድብ ለ4ኛ ዙር የፈፀሙት የቦንድ ግዢ ርክክብ ፕሮግራም ተካሂዷል።

በመርሃ ግብሩ ንግግር ያደረጉት የጂንካ ዩኒቨርስቲ ፕሬዚዳንት ኩሴ ጉድሼ(ዶ/ር) በሀገር አቀፍ ደረጃ የህዳሴውን ግድብ ለማጠናቀቅ የመጨረሻው ምዕራፍ የሀብት ማሰባሰብና የቦንድ ሽያጭ መርሃግብር እየተካሄደ እንደሚገኝ ተናግረው፤ ግድቡ ሀገራዊ አንድነታችንን፣ በራስ አቅም የመልማት ደረጃችንን የለየንበትና የኢትዮጵያን የወደፊት እጣ ፈንታ ያረጋገጥንበት ነው ብለዋል።

ፕሬዚዳንቱ አክለውም ግድቡ ላለፉት ጊዜያት በአለም አቀፍ ደረጃ ለኢትዮጵያ ከልማትና ከኢኮኖሚያዊ ጥቅም ባሻገር ፖለቲካዊ ጉዳይ ጭምር ሆኖ ሲዘወር እንደነበር አስታውሰው፤ መላው ኢትዮጵያውያን በጋራ ተቀናጅተው አልበገርነታቸውን ያስመሰከሩበትና የዩኒቨርሲቲው ሠራተኞችም በዚህ ሁሉ ላሳዩት ድጋፍና አጋርነት አመሰግነዋል።

በጂንካ ዩኒቨርስቲ የሥራ አመራር ቦርድ ጽ/ቤት ኃላፊና የህዳሴ ግድብ ግንባታ ሀብት አሰባሰብ አስተባባሪ መምህር አምባ ጩፋ፤ በ2017 በጀት አመት ለታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ማጠናቀቂያ በተካሄደው የአራተኛው ዙሪያ ሀብት አሰባሰብ 1 ሚሊዮን 5 መቶ ሁለት ሺህ ብር መሰብሰቡን ጠቁመው፤ ለመምህራንና ለአስተዳደር ሠራተኞች የቦንድ ርክክብና የምስጋና ፕሮግራም መደረጉን አንስተዋል።

በቦንድ ግዢ ላይ የተሳተፉ መምህራንና አስተዳደር ሠራተኞችም የግድቡ ግንባታ ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ ድጋፍ እያደረጉ መቆየታቸውን አስታውሰው፤ በአሁኑ ወቅት በተደረገው የቦንድ ግዢ የግድቡን ግንባታ ለማጠናቀቅ በሚደረገው ርብርብ ውስጥ አሻራቸውን በማስራፈቸው ደስተኛ መሆናቸውን ጠቁመዋል።

ዘጋቢ፡ ጄታ ታገሠ – ከጂንካ ጣቢያችን