ኃይለማርያም እና ሮማን ፋውንዴሽን የአርብቶ አደሩን የግብርና ትራንስፎርሜሽን በማሳደግ የተፈጥሮ እና የእንስሳት ሀብቶችን በተገቢው አዘምነው እንዲጠቀሙ ለማስቻል እየሠራ መሆኑን ገለፀ

የኃይለማርያም እና ሮማን ፋውንዴሽን ኘሮጀክቱ በሚሰራቸው ዘርፎች ዙሪያ ሥራ ለመጀመር የሚያስችል ስልጠና ለሚዲያ ባለሙያዎች በጂንካ ከተማ ሰጥቷል።

የደቡብ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ድርጅት ጂንካ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት ተወካይ አቶ ዳኜ ጥላሁን፤ ፋውንዴሽኑ በአርብቶ አደሩ አካባቢ በሚሰራቸው የግብርና ትራንስፎርሜሽን ሥራዎች ተደራሽነታቸውን ይበልጥ በማስፋት የአርብቶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እየሠራ ያለውን ሥራ በሚዲያ ተደራሽ ለማድረግ ምርጫቸው ስላደረጉ አመስግነዋል።

አክለውም ጋዜጠኞችም በተዘጋጀው ስልጠና መሰረት ተግባራቱን በዕውቀት ለመስራት እንዲያስችል የነቃ ተሳትፎ እንዲያደርጉ አሳስበዋል።

የኃይለማርያም እና ሮማን ፋውንዴሽን የግብርና የምግብና የሥነ-ምግብ ዋስትና ኘሮጀክት አስተባባሪ አቶ ተስፋዬ ፋላአ፤ ፋውንዴሽኑ በደቡብ ኦሞ በ5 ቋንቋዎች ማለትም በበና፣ ፀማይ፣ ሐመር፣ ዳሰነች፣ ኛንጋቶም ቋንቋዎች በግብርና ትራንስፎርሜሽን ብሎም የምግብና ሥነ- ምግብ ዋስትና ኘሮጀክት ትልቁ ግብ በአካባቢው ያለውን የተፈጥሮና የመሬት አቅም፣ የእንስሳት ልማትና እምቅ ሀብቶችንና ሌሎችንም ማህበረሰቡ እንዲጠቀም ኘሮጀክቱ ይሰራል ብለዋል።

ኘሮጀክቱ የህብረተሰቡን ግንዛቤ በመጨመር መደረግ የሚገቡ የግብርና ተግባራትን ጥቅም ላይ መዋል ስለሚገባቸው የእርሻ መሬቶች፣ የውሃ አማራጮች እና ሌሎችንም ፀጋዎች በአግባቡ ተጠቅሞ የግብርና ትራንስፎርሜሽን ውስጥ እንዲገባ ማስቻልን ያለመ ነው ሲሉም ተናግረዋል።

የግንዛቤ መድረኩ ምርትና ምርታማነትን በመጨመር ረገድ የሥነ-አመጋገብና የሥነ-ምግብ ዋስትናን በማህበረሰቡ ዘንድ ከማረጋገጥ አኳያ የግብርና ምርቶች ግብይት ትስስርን ከመፍጠር እና ጎጅ ልማዳዊ ድርጊቶችን ከመከላከል አኳያ የተያዙ ተግባራት ተደራሽ እንዲሆኑ ለማስቻል ነው ብለዋል።

ለእነዚህ ተግባራት ተደራሽነት ዋነኛው ሚዲያ እንደመሆኑ ድርጅቶችና ግለሰቦች የማይደርሱባቸውን የህብረተሰብ ክፍሎች የማድረስና መልዕክቶችን የማስተላለፍ እና ለውጥ የማምጣት አቅም ያለው ተቋም በመሆኑ ለባለሙያዎች ስልጠና መስጠት ማስፈለጉን ገልፀዋል።

ስልጠናውን ያገኙ የሚዲያ ባለሙያዎችም በግብርና በሥነ-ምግብ እና የእንስሳት ሀብት አጠቃቀምን በዘመነ መንገድ ሀብቱን በማልማት ተጠቃሚነታቸውን እንዲያረጋግጡ እንደ ሚዲያ ባለሙያ የበኩላቸውን ሚና እንደሚወጡ ተናግረዋል።

ዘጋቢ: ከተማ በየነ – ከጂንካ ጣቢያችን