የደቡብ ድምፅ ሬዲዮ ኤፍ ኤም 100.9 ጣቢያ መመስረት የብሔር ብሔረሰቦችን ባህል እና ቋንቋ በማሳደጉ ረገድ ከፍተኛ ሚና መጫወቱን የሀዲያ ዞን የኪነት ቡድን አባላት ተናገሩ

የኪነት ቡድን አባላቱ ለ20ኛዉ ዓመት የ100.9 ኤፍ ኤም የምስረታ በዓል የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክትም አስተላልፈዋል።

በ1997 ዓ.ም  የካቲት 23 አሃዱ ብሎ የ3 ሰዓት  የአየር ላይ ቆይታ ስርጭቱን የጀመረው የደቡብ ድምፅ ኤፍ ኤም 100.9 ሬዲዮ ለህብረተሰቡ ወቅታዊ መረጃዎችን በማድረሱ ረገድ የድርሻውን እያበረከተ ይገኛል።

የሬዲዮ ጣቢያው መመስረት የብሔር ብሔረሰቦችን ቱባ ባህሎችን በማስታዋወቁ ረገድ ከፍተኛ ሚና መጫወቱን ከሀዲያ ዞን የኪነት ቡድን አባላት መካከል ሙሳ ኤርቤቶ ተስፋዬ አበበ እና ታምራት ሀሊል ተናግረዋል ።

የብሄር ብሄረሰቦችን ሙዚቃዎች  ቀርጾ ለህዝብ ጆሮ እንዲደርስ በማድረጉ ረገድም የሬዲዮ ጣቢያው በኪነጥበቡ ረገድ አስተዋጽኦው ከፍተኛ መሆኑን ገልጸዋል ።

ጣቢያው በቀድሞ የደቡብ ብሄር ብሄረሰቦች እና ህዝቦች ክልል ውስጥ የነበሩ የ56 ብሔር ብሔረሰቦች የቱሪስት መስቦችን በማስተዋወቅ ረገድም የላቀ ሚና መጫወቱን ጠቅሰዋል ።

የቀድሞ ደቡብ ክልል በአራት ክልሎች ሲደራጅ የ4ቱ ክልሎች የጋራ ሀብት ሆኖ መቀመጫውን ሀዋሳ ያደረገው የደቡብ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ድርጅት አሁን ላይ በኤፍ ኤም 100.9 በደቡብ ቴሌቪዥን እንዲሁም በ12  ቅርንጫፍ ጣቢያዎችና በአዲስ አበባ ማቀባበያ ጣቢያ አማካይነት ለህብረተሰቡ አስተማሪ አዝናኝና ለልማት ቀስቃሽ የሆኑ መረጃዎችን እያደረሰ ይገኛል።

በቅርንጫፍ ጣቢዎች  በ50 የብሔር ብሔረሰቦች ቋንቋዎች የሚዲያ አገልግሎት እየሰጠ ይገኛል።

በህትመት ሚዲያውም የንጋት ጋዜጣና በሳይበር ሚዲያ አውታር   ለአንባቢያን መረጃዎችን እየተሰራጨ ይገኛል ።

ዘጋቢ : ተሻለ ከበደ -ከሆሳዕና ጣቢያችን