ብልፅግና ፓርቲ የሠላም፣ የልማት እና መልካም አስተዳደር ጉዳዮችን ከቃል ባሻገር መሬት ላይ የሚታዩ የተለያዩ

ተግባራትን በተጨባጭ እየሠራ እንደሚገኝ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የቴክኒክና ሙያ ትምህርትና ስልጠና ቢሮ ኃላፊ አቶ አሠፋ ደቼ ተናገሩ

”ብልፅግና መፍጠን እና መፍጠር ለጉባኤያችን ውሳኔዎች ስከታማነት” በሚል መሪ ቃል በ2ኛው ዙር የብልፅግና ፓርቲ ውሣኔዎችና አቅጣጫዎች ላይ በሣጃ ከተማ እና ዙሪያው ካሉ ነዋሪዎች ጋር ውይይት ተካሂዷል።

በመድረኩ ላይ በእንግድነት የተገኙት የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የቴክኒክና ሙያ ትምህርትና ስልጠና ቢሮ ኃላፊ አቶ አሠፋ ደቼ፤ የተለያዩ ሥራ ዕድሎችን በመፍጠር ፈጥኖ ወደ ተግባር ለመግባት አንድነትን እና ሠላምን ማምጣት ያስፈልጋል ብለዋል።

በ2ኛው ዙር የፓርቲ ውሣኔዎችና አቅጣጫዎች ላይ የተቀመጡ ጉዳዮች በዚህ ውይይት ብቻ የሚበቁ አይደሉም ያሉት ኃላፊው፤ ቀጣይ ሕዝቡን በማሣተፍ በየደረጃው የሚገኙ ባለድርሻ አካላት ጋር እየተነጋገርን እንሠራለን ብለዋል።

በቀጣይ ሦስት ዓመታት ግጭትን በማስቆም ሠላማዊ የሆነ ሀገር እና ክልል መፍጠር እንደሚያስፈልግ ነው የተናገሩት፡፡ በዚህም ሕዝቡ መደገፍ እንዳለበትም አሣስበዋል።

የየም ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ሽመልስ እጅጉ በበኩላቸው ሣጃ ከተማን ለማልማት እና ለማሳደግ እየተሠሩ ያሉ የመልካም አስተዳደር ስራዎች እና ሕብረተሰቡን የሚጠቅሙ ተግባራት ላይ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑን አስረድተዋል።

ከተማዋን ለማሣደግ እየተሰሩ ካሉ ተግባራት መካከል የኮሪደር ልማት አንዱ ሲሆን ቤታቸውን አፍርሰው እንደገና ገንዘብ አዋጥተው እያለሙ ያሉ ነዋሪዎችን አመስግነዋል።

እስካሁን ባለው ሂደት 62 ሚሊዮን ብር በላይ ሀብት ተሰብስቦ ተግባር ላይ መዋሉን አስረድተዋል።

ፓርቲው ያስቀመጣቸው የትምህርት፣ የጤና፣ የግብርናና መሠል ተግባራት ላይ ተጠናክሮ በመሥራት ብልፅግናን ማምጣት ያስፈልጋል ብለዋል።

ሕዝብን የሚያማርሩ ችግሮችን በተለይም አገልግሎት አሰጣጥን በማዘመን ለወጣቶች እና ሴቶች ሥራ ዕድል መፍጠር ላይ መታገል ያስፈልጋልም ብለዋል።

አራት ሚሊዮን ብር በላይ ተሰብስቦ ለመፅሐፍ ህትመት መብቃቱን የተናገሩት አቶ ሽመልስ፤ የከተማዋን ውሃ ችግር ለመቅረፍ ከ74 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ ቁፋሮ እየተጀመረ ይገኛል ብለዋል።

የመድሃኒት እና የግብአት ችግሮችን ለመፍታት እንሠራለን ያሉት አቶ ሽመልስ፤ ሕዝቡ እየተሠሩ ያሉ ሥራዎችን በመደገፍ ወደ ብልፅግና ማሻገር አለበት የሚል መልዕክት አስተላልፈዋል።

በመድረኩ መወያያ ፅሁፍ ያቀረቡት የሣጃ ከተማ ከንቲባ አቶ ጌታሁን ካሣሁን የውሃ፣ የመብራት እና መሰል ችግሮችን ለመፍታት እንሠራለን ብለዋል።

የከተማዋን መሠረታዊ ችግሮችን ለመቅረፍ ፕላን ዝግጅት ተጠናቅቆ ወደ ተግባር እየተገባ መሆኑን አስረድተዋል።

የከተማዋ ልማት፣ ዕድገት እና መልካም አስተዳደር ጉዳዮችን መፍታት የሚቻለው የሕብረተሰቡ አንድነት ሲፈጠር በመሆኑ አንድነታችንን ማጠናከር ያስፈልጋል ብለዋል።

በውይይቱ ላይ የተገኙት የሣጃ ከተማ እና ዙሪያው ያሉ ነዋሪዎች በሰጡት አስተያየት በከተማዋ በርካታ የልማት እና መልካም አስተዳደር ሥራዎች እየተከናወኑ በመሆኑ ተግባራቱ ተጠናክረው መቀጠል እንዳለባቸው ገልፀው፤ በኮሪደር ልማቱ ስራ ደስተኞች መሆናቸውን አክለዋል፡፡

የመብራት፣ የውሃ እና የሥራ ዕድል ፈጠራ እንዲሁም ሰላም ላይ አሁንም ትኩረት ተሠጥቶ መሠራት እንደአለበት አስተያየት ሰጪዎች ተናግረዋል፡፡

ዘጋቢ፡ ማሙዬ ፊጣ – ከወልቂጤ ጣቢያችን