ዲግሪው “ወረቀት ብቻ ሳይሆን፣ የሀገር ተስፋና የትውልድ ኃላፊነት ነው” – አፈወርቅ ካሱ (ፕ/ር)

ሀዋሳ፡ ሰኔ 20/2018 ዓ.ም (ደሬቴድ) ዲግሪው “ወረቀት ብቻ ሳይሆን፣ የሀገር ተስፋና የትውልድ ኃላፊነት ነው” ሲሉ የቦንጋ ዩኒቨርሲቲ አስተዳደር ቦርድ ሰብሳቢ አፈወርቅ ካሱ (ፕ/ር) ገለጹ፡፡

የቦንጋ ዩኒቨርሲቲ በተለያዩ የትምህርት መስኮች ያስተማራቸውን 257 ተማሪዎችን በዛሬው ዕለት አስመርቋል፡፡

በመርሃ-ግብሩ ላይ የተገኙት የቦንጋ ዩኒቨርሲቲ አስተዳደር ቦርድ ሰብሳቢ አፈወርቅ ካሱ(ፕ/ር)፣ ዕለቱ ለተመራቂዎች የፅናት፣ የትጋትና የመስዋዕትነት ዕለት መሆኑን ገልጸዋል፡፡

ቦንጋ ዩኒቨርሲቲ በተለይ በእንስሳት ህክምና ዶክትሬት ለመጀመሪያ ጊዜ ማስመረቅ መቻሉ የሚያኮራ ነው ብለዋል፡፡

ከተመራቂ ተማሪዎች መካከል አብዛኞቹ ብሄራዊ የመውጫ ፈተና ማለፋቸው አበረታች ውጤት መሆኑን ገልጸው ስኬቱ የሁሉም ባለድርሻ አካላት የጥረት ውጤት ነው ብለዋል፡፡

ኢትዮጵያ በብዙ መልኩ ለውጥ እያደረገች ስለመሆኗ ጠቁመው በዚህ ረገድ ከተመራቂ ተማሪዎች ብዙ እንደሚጠበቅ ነው የገለጹት፡፡

ተመራቂዎች ባገኙት ዕውቀት ሥራ ፈጣሪዎች እንዲሆኑ መክረዋል፡፡

የእውቀት ባለቤት መሆን የማህበረሰብ ኃላፊነትን መውሰድ ይጠይቃል ያሉት ፕሮፌሰር አፈወርቅ ካሱ፤ ለሀገር ሰላም እና አንድነት መሥራት ይጠበቃል ብለዋል፡፡

ተመራቂዎች የተቀበሉት ዲግሪ “ወረቀት ብቻ ሳይሆን፣ የሀገር ተስፋና የትውልድ ኃላፊነት ነው” ሲሉ ገልጸዋል፡፡

ለተመራቂ ተማሪዎች እና ለቤተሰቦቻቸው እንዲሁም ለመላው የዩኒቨርሲቲው ማህበረሰብ የእንኳን ደስ አላችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡

ለ8ኛ ዙር በተካሄደው የምረቃ መርሃ-ግብር ላይ የክልልና የዞን ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች እና የተማሪ ወላጆች ተገኝተዋል፡፡

ዘጋቢ: ዳንኤል መኩሪያ – ከቦንጋ ጣቢያችን