የደመራ እና ኢሬቻ በዓላት እሴቶቻቸውን ጠብቀው እንዲከበሩ ወጣቶች የበኩላቸውን ሚና ሊወጡ ይገባል – ከንቲባ አዳነች አቤቤ

የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ እና የአዲስ አበባ ከተማ ብልፅግና ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ መለስ አለሙ በሀገራዊ ወቅታዊ ጉዳይ፣ በደመራ እና በኢሬቻ በዓላት አከባበር ዙሪያ ከሁሉም ክፍለ ከተሞች ከተውጣጡ ወጣቶች ጋር ተወያይተዋል።

ከንቲባ አዳነች አቤቤ የደመራ እና የኢሬቻ በዓላት ሃይማኖታዊና ባሀላዊ እሴቶቻቸውን ጠብቀው እንዲከበሩ ለማድረግ ወጣቶች ሚና የላቀ መሆኑን ተናግረዋል።

ወጣቶች ከፀጥታ አካላት ጋር በቅንጅት በመስራት ደመራ እና የኢሬቻ በዓላትን ኢትዮጵያዊ ጨዋነት እና ሃይማኖታዊ እሴቶችን በጠበቀ መልኩ ዓለም አቀፍ ጫና ተቋቁመን ማክበር እንደምንችል በተግባር ማሳየት ይኖርብናል ብለዋል።

ከንቲባ አዳነች አያይዘውም ጠላቶቻችን የሚመጡበትን መንገድ ማወቅና የተላላኪዎቻቸውን የአሸባሪው ህወሓትና ሸኔ እኩይ ተግባራትን መረዳት እንደሚገባም አመላክተዋል፡፡

አሸባሪ ቡድኖቹ የመስቀል ደመራ እና የኢሬቻ በዓላት በሰላም እንዳይከበሩ የሚያደርጉትን የጥፋት እንቅስቃሴ ከፀጥታ አካላት ጋር በቅንጅት በማጋለጥ በዓላቱ ሃይማኖታዊና ህዝባዊ መሠረታቸውን ጠብቀው በሰላም እንዲከበሩ ለማድረግ ወጣቶች የበኩላቸውን ሚና ሊወጡ እንደሚገባ አሳስበዋል።

ባለፈው ዓመት ከ400 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ወጣቶች የስራ እድል መፈጠሩን የጠቀሱት ከንቲባዋ ÷ ሀገሩን የሚለውጥና አምራች ወጣት ለመፍጠር ከተማ አስተዳደሩ ለትውልድ ግንባታ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል።

የውይይቱ ተሳታፊ ወጣቶ በበኩላቸው÷ የደመራ እና የኢሬቻ በዓላት በወንድማማችነት በማክበር በሰላም ተከብረው እስከሚጠናቀቁ አንዳችን ለአንዳችን ዘብ በመቆም እና የጥፋት ሃይሎችን በማጋለጥ ለመስራት ዝግጅት አድርገናል ማለታቸውን ከኮልፌ ቀራኒዮ ኮሙኒኬሽን ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡