የቴክኒክና ሙያ ተቋማት በሀገር ኢኮኖሚ ዕድገት ላይ የበኩላቸውን እንዲያበረክቱ በትብብር መስራት እንደሚገባ የኢፌዲሪ ስራና ክህሎት ሚኒስትር አስታወቀ
ሀዋሳ፡ ሕዳር 20/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) የቴክኒክና ሙያ ተቋማት ከስልጠና ባሻገር በየአካባቢው ያሉ እምቅ ፀጋዎችን ወደ ሀብት በመቀየር በሀገር ኢኮኖሚ ዕድገት ላይ የበኩላቸውን እንዲያበረክቱ በትብብር መስራት እንደሚገባ የኢፌዲሪ ስራና ክህሎት ሚኒስትር አስታውቋል።
በሚኒስቴር መስሪያ ቤቱና በተባባሪ ባለድርሻ አካላት የተመራ ልዑካን ቡድን የሆሳዕና ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ የስራ እንቅስቃሴ ሂደት ጎብኝቷል።
ጉብኝቱን የመሩት በኢፌዲሪ ስራና ክህሎት ሚኒስቴር የቴክኒክና ሙያ ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ ዶ/ር ተሻለ በሬቻ፤ በሀገሪቱ ባለፉት ዓመታት የተጀመሩ የሪፎርም ስራዎችን መነሻ በማድረግ የተቋማትን የስራ እንቅስቃሴ፣ የክህሎት ልማት፣ የቴክኖሎጂ ሽግግር ሂደቶችን መቃኘት አስፈላጊ ሆኖ በመገኘቱ ጉብኝቱ መዘጋጀቱን ገልፀዋል።
በየአካባቢው ያሉ የቴክኒክና ሙያ ተቋማት ያሏቸውን እምቅ ፀጋዎችን ወደ ተግባር በመለወጥ በሀገር ኢኮኖሚ መሻሻል ላይ የበኩላቸውን መወጣት እንደሚገባቸው የጠቆሙት ሚኒስትር ዴኤታው ኮሌጁ በክህሎት ልማትና አምራቾችን ወደ ኢንተርፕራይዝ ደረጃ በማሸጋገር ረገድ የጀመራቸውን ተግባራት በላቀ ሁኔታ ማስቀጠል ይገባል ብለዋል።
የሆሳዕና ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ ዲን የሆኑት አቶ አወል ሸንጎ በበኩላቸው፤ ኮሌጁ ከባለፉት ጊዜያት ጀምሮ ብቁና ተወዳዳሪ የሆኑ ዜጎችን በማፍራት የአካባቢን ችግር መቅረፍ የሚችሉ የፈጠራ ስራዎችን ተደራሽ በማድረግና በሌሎች መስኮችም የተጣለበትን ኃላፊነት እየተወጣ ስለመሆኑ አስረድተዋል።
የተቋሙን የውስጥ ገቢ በማሳደግ ከመንግሥት ጥገኝነት ለማላቀቅ ራዕይ ሰንቆ እየሰራ መሆኑን ያነሱት አቶ አወል በተለይም በግብርና፣ በአረንጓዴ ልማት፣ በጨረቃ ጨርቅና በልዩ ልዩ ዘርፎች የሚያጋጥሙ ችግሮችን በመቅረፍ አምራቾችን ወደ ኢንተርፕራይዝ ደረጃ በማሻገር አበክሮ እየሰራ ነው ብለዋል።
በጉብኝቱ የተካፈሉት የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ስራ ዕድል ፈጠራና ኢንተርፕራይዝ ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ሙስጠፋ ኢሳ እና የክልሉ ቴክኒክና ሙያ ትምህርትና ስልጠና ቢሮ ኃላፊ አቶ አሰፋ ዶቼ በጋራ በሰጡት አስተያየት፤ ኮሌጁ የተቋሙን ዲጅታላይዜሽን ስርዓት በማዘመን ከስልጠና ባሻገር ወደ ተግባር በመለወጥ ሂደትና ምቹና ሳቢ ገጽታ ከመፍጠር ጋር በተያያዘ እያሳየ ባለው የስራ እቅስቃሴ መደሰታቸውን ገልፀዋል፡፡
ይህንንም አጠናክሮ በማስቀጠልና በማስፋፋት ለሀገር ኢኮኖሚ ዕድገት መጎልበት የበኩሉን ድርሻ እንዲወጣ ሁሉም መረባረብ ይገባል ብለዋል።
ዘጋቢ: ሄኖስ ካሳ – ከሆሳዕና ጣቢያችን

More Stories
በአንድ ጀምበር 800 ሚሊየን ችግኝ ተከላ አካል የሆነው 8ኛው ምዕራፍ የአረንጓዴ አሻራ በኣሪ ዞን ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች ተከላ እየተካሄደ ነው
በኣሪ ዞን በ1 ጀንበር 4.9 ሚሊዮን ችግኝ የመትከል የአረንጓዴ አሻራ ዘመቻ እየተካሄደ ይገኛል
በዘንድሮ አንድ ጀምበር ችግኝ ተከላ መርሀ-ግብር ከ 21 ሚሊዮን በላይ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች እንደሚተከሉ የጋሞ ዞን ግብርና መምሪያ አስታወቀ