በሀድያ ዞን በሆመቾ ከተማ አስተዳደር ለሚኖሩ ለ3 ሺህ አቅመ ደካማ ቤተሰብ ተማሪዎች ከአንድ ሚሊየን ብር በላይ የሚገመት የትምህርት ቁሳቁስ  ድጋፍ  ተደረገ

የትምህርት ቁሣቁስ ድጋፉ በውጭ ሀገራት የሚኖሩ ”ፍሬንድስ ኦፍ ሆመቾ ” የሆመቾ ተወላጆች በጎ አድራጊ ማህበር የተደረገ ነው።

አቶ አረጋ በዶሬ የፍሬንድስ ኦፍ ሆማቾ ግብረ-ሰናይ ድርጅት መሥራችና ሥራ አስኪያጅ ሲሆኑ ድርጅቱ በተለያዩ መሠረተ-ልማት ሁነቶች ላይ ትኩረት አድርጎ የሚሰራ ነው ብለዋል።

ድርጅቱ ከዚህ ቀደም ለጤና አገልግሎት የሚሆኑ ቁሳቁሶችን ጨምሮ የትምህርት ቤቶች እድሳትና ውሃ መሥመር ዝርጋታ ሥራዎች በሰፊ ማከናወኑን ተናግረዋል።

በዕለቱም ከሆማቾ ከተማ አስተዳደርና ጊቤ ወረዳ ለተወጣጡ ለ3 ሺህ አቅመ-ደካማ ተማሪዎች የደብተርና ብዕር ድጋፍ መደረጉን አብራርተዋል።

የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ የሚሰሩ ግብረ-ሰናይ ድርጅቶች አበርክቶ ጉልዕ በመሆኑ በመንግሥት ልታገዙ እንደሚገባ የተናገሩት ደግሞ የሆማቾ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ምስጋና አለሙ ናቸው።

ተማሪዎች በተደረገላቸው ድጋፍ በርትተው በመማር ተወዳዳሪና ግንባር-ቀደም እንዲሆኑ ጥሪ አስተላልፈዋል።

ድጋፍ የተደረገላቸው ተማሪዎች ባገኙት የትምህርት ቁሳቁስ መደሰታቸውን ገልፀው፣ የተሻለ ውጤት ለማምጣት በርትተው እንደሚማሩ  ተናግረዋል።

ዘጋቢ:- አብርሃም ሙጎሮ ከሆሳዕና ጣቢያችን