ጳጉሜን 5 – የነገ ቀን “የዛሬ ትጋት፤ ለነገ ትሩፋት” በሚል መሪ ቃል በወላይታ ሶዶ ከተማ በእግር ጉዞ ተከበረ

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል መንግስት የፐብሊክ ሰርቪስና የሰው ሀብት ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ንጋቱ ዳንሳ የመድረኩን ዓላማ ሲገልጹ ተስፋ ያላት እና የበለጸገች ኢትዮጵያን ለትውልድ ማስረከብን እንደሆነ በመግለጽ ወጣቱ በኃላፊነት ስሜት የነገ ሀገር እንዲረከብ ጠይቀዋል።

በመድረኩም በዛሬው ቀን የቀረቡ ወጣቶች ኃላፊነት መሸከም የሚችል ወጣት ያለን መሆኑን አረጋግጠውልናል ብለዋል አቶ ንጋቱ ዳንሳ።

በጋራ አቋማችሁ አገር እንዲህ ናት የሚል መልዕክት አስተላልፋችኋል ያሉት የቢሮው ኃላፊ እጅ ለእጅ ተያይዘን የተጀመረውን ብልጽግና የምናስቀጥልበት ይሁን ሲሉ መልካም ምኞታቸውን ገልጸዋል።

የወላይታ ዞን ምክትል አስተዳዳሪ አቶ ዳንኤል ደሌ ጳጉሜን 5 የነገ ቀን ከዛሬው ፕሮግራም ዝግጅት ብዙ ተምረናል ሲሉ በመግለጽ እኛ ከአባቶቻችን የተረከብናትን ውብ ሀገር ለቀጣይ ትውልድ የተሻለች ሀገር የምናስረክብበት ልጆች የማስቀጠል ኃላፊነት የሚረከቡበት ነው ብለዋል።

በመድረኩ በህጻናትና ወጣቶች የተዘጋጁ የተለያዩ ትርዕቶችና ዝግጅቶች የቀረቡ ሲሆን የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የወጣቶች ሊግ ጽ/ቤት ከወላይታ ዞን ወጣቶች ሊግ ጽ/ቤት የተማሪ መጻህፍት ለወላይታ ዞን ትምህርት መምሪያ የማስረከብ እንዲሁም ለህጻናት ሰንደቅ ዓላማ የማስረከብ ሥነሥርዓት ተካሂዷል።

ዘጋቢ፡ በቀለች ጌቾ – ከዋካ ጣቢያችን