በመጽሐፍ ቅዱስም ሆነ በቅዱስ ቁራን ፈጣሪ የሰው ልጅ ጥሮ ግሮ እንዲበላ ደንግጓል ያሉን የዳውሮ ኮንታ ሀገረ ስብከት ስራ አስኪያጅ መላከ ሀይል ቆሞስ አባ ክንፈ ገብርኤል ገበየሁ፤ የሰው ልጆች የሆንን ሁላችንም በተሰጠን መክሊት ራሳችንን፣ ቤተሰቦቻችንን ብሎም ሀገራችንን ሰርተን በሚፈለገው ልክ መቀየር ስንችል ነገር ግን በስንፍና ተተብትበን ወደኋላ እየቀረን እንገኛለን ብለዋል።
ስለሆነም በአዲሱ ዓመት በተለይ ወጣቱ ከስንፍናው ተላቆ በየተሰማራበት የስራ መስክ ሁሉ ጠንክሮ ውጤታማ እንዲሆን አባታዊ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።
በዞኑ የእስልምና ጉዳይ ምክትል ሰብሳቢና ኢማም የሆኑት ሼክ ከሊፋ ዓሊ አባ ስመሊ በበኩላቸው የሰው ልጅ በተሰማራበት የስራ መስክ በታማኝነትና በትጋት ስራውን መወጣት ሲችል ነው ፈጣሪን ማክበር የሚችለው፡፡ ስለሆነም በአዲሱ ዓመት እንደእምነቱ ተከታይ፣ አላህን ለማስደሰት ሁሉም ጠንክሮ መስራትና ለለውጥ መትጋት ይኖርበታል ብለዋል።
ስንፍና የኃጢያት ምንጭ እንደሆነ የተናገሩት ደግሞ በካቶሊክ ቤተክርስቲያን የታርጫ ቅዱስ ዮሴፍ ቆሞስ የሆኑት አባ ላቢኔ እና በፕሮቴስታንት እምነት የቃለ-ህይወት ቤተክርስቲያን ወንጌላዊ ቶማስ ኡታ በሰጡት የጋራ አስተያየት፤ ከርሃብና ዕርዛት ለመወጣት ተማሪው በትምህርቱ፣ አርሶ አደሩም በእርሻውና ሌላውም እንደዚሁ በተሰማራበት ስራ ሁሉ ባለው ችሎታና አቅም በመትጋት ስራውን ሰርቶ በአዲሱ ዓመት መበልጸግ ይኖርበታል ሲሉ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።
በመጨረሻም ሁሉም የኃይማኖት አባቶች የ2017 አዲሱ ዓመት የፍቅር፣ የሠላም፣ የፍሰሃ እንዲሁም መልካም የስራ ዘመን እንዲሆን ሲሉ የተመኙ ሲሆን በተፈጥሮም ሆነ በሰው ሰራሽ አደጋ ምክንያት ከቤት ንብረታቸው ለተፈናቀሉትና አደጋም ለደረሰባቸው ብሎም ህይወታቸውን ላጡት ወገኖች ሁሉ ፈጣሪ ምህረቱን እንዲያወርድ ሲሉ ተማጽነዋል።
አዘጋጅ፡ አሸናፊ ግዛው – ከዋካ ጣቢያችን

More Stories
የሴቶች ወጣቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ቋሚ ኮሚቴ በስፖርትና ባህል ልማት ዘርፍ የሚገኘውን ተጠቃሚነት ለማሳደግ አበክሮ መስራት እንደሚገባ ተገለጸ
ህግና አስተዳደራዊ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የክልሉን ፍትህ ቢሮ የ2018 በጀት ዓመት የ6 ወራት ሥራ አፈፃፀም አደመጠ
ከተማዋን ለነዋሪዎች ምቹ ለማድረግ እንደሚሠራ የዲላ ከተማ አስተዳደር አስታወቀ