የክረምት በጎ ፍቃድ አገልግሎት በበጋም ተጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባ ተገለጸ

ሀዋሳ: ነሐሴ 30/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) በክረምት ወራት የተጀመሩ የበጎ ፍቃድ አገልግሎት ሥራዎች በበጋ ወራትም ተጠናክረው ሊቀጥሉ እንደምገባ ተገልጿል።

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ማህበራዊ ክላስተር ጂንካ ማዕከል የሴቶች ሊግ አባላት “በጎነት ለእህተማማችነት፤ ለትውልድ ግንባታና ዘላቂ ልማት” በሚል መሪ ቃል የበጋ ወራት በጎ ፍቃድ ማብሰሪያ ኮንፈረንስ በጂንካ ከተማ አካሂደዋል።

የአሪ ዞን ብልጽግና ፖርቲ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ግዛቸው በላይ ለኮንፈረንሱ ተሣታፊዎች የእንኳን ደህና መጣችሁ መልዕክት ባስተላለፉት ወቅት፤ ፖርቲው በዋናነት ሰው ተኮር ለሆኑ ጉዳዮች ቅድሚያ ሰጥቶ እየሠራ እንዳለ ጠቁመው ከእነዚህም አንዱ የበጎ ፍቃድ አገልግሎት ነው ብለዋል።

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት ሴቶች ሊግ ኃላፊ ወ/ሮ እቴነሽ በየነ በበኩላቸው በተያዘው ክረምት ወራት ክልል አቀፍ የበጎ ፍቃድ አገልግሎት በሴቶች የአረጋዊያን ቤት እድሳት፣ የደም ልገሳ፣ ለአቅመ ደካማ ቤተሰብ ተማሪዎች የመማሪያ ቁሳቁስ ድጋፍ ማሰባሰብ እና ሌሎች ሰብዓዊ ድጋፎች ሲደረጉ እንደነበር አመላክተዋል።

በመጠናቀቅ ላይ ባለው የክረምት ወራት የበጎነት ተግባር በሁሉም አካባቢ ከቀድሞው የተሻለ የሰበዓዊነት፣ የመደጋገፍና የመረዳዳት ባህል የታየበት ነው ያሉት ኃላፊዋ በቀጣይ የበጋ ወራትም ሳይቀዛቀዝ ይህንን አጠናክሮ ማስቀጠል ይጠበቃል ብለዋል።

በመድረኩ የክላስተሩ የ2016 በጀት ዓመት እቅድ አፈጻጸም እና የ2017 እቅድ ቀርበው ውይይት ተደርጎባቸዋል።

ዘጋቢ: ታገል ለማ – ከጂንካ ጣቢያችን