የኮሬ ልማት ማህበር ጠቅላላ ጉባዔውን አካሄደ

ጉባኤውን በንግግር የከፈቱት የኮሬ ዞን የመንግሥት ዋና ተጠሪና የኮሬ ልማት ማህበር ቦርድ ሰብሳቢ አቶ ጢሞቲዎስ በቀለ ማህበሩ በቆይታው ካጋጠመው ጥንካሬም ሆነ ጉድለት ትምህርት ወስደን በቀጣይ የማህበሩን ህልውና ለማስቀጠል የሚያቅተን የለም ብለዋል።

የኮሬ ዞን አስተዳዳሪ አቶ ታረቀኝ በቀለ በበኩላቸው ከምሥረታው ጀምሮ ብዙ ችግር አልፎ የመጣ ማህበር እንደሆነ በማስታወስ ለዘላቂ ልማት በቀጣይ በየደረጃው የሚገኙ መዋቅሮች እጅ ለእጅ በመያያዝ የድርሻውን ሊወጡ እንደሚገባ አብራርተዋል።

የማህበሩ ሥራ አስኪያጅ አቶ ዳግም ታደሰ የአፈፃፀም ሪፖርት ባቀረቡበት ወቅት በማህበረሰቡ ውስጥ ሥር ሰደው የሚገኙ የልማት ማነቆዎችን በመለየት ከማህበረሰቡ፣ ከመንግሥትና አጋር ድርጅቶች ጋር በመተባበር ዘላቂ የልማት ፖሊስዎችን በመንደፍ ህብረተሰቡን በማነቃነቅና ወደ ትግበራው በማስገባት ህብረተሰቡን የልማቱ ተጠቃሚ ማድረግ ይጠበቅብናል ብለዋል።

የማህበሩ ኦዲት ሪፖርት በዞኑ የሥነ-ምግባርና ፀረ-ሙስና ቡድን መሪ እና የልማት ማህበሩ የኦዲት ሰብሳቢ አቶ ደፋዩ ዳካ ቀርቦ አስተያየት ተሰጥቶበታል።

ከጉባኤው ተሳታፊዎች አቶ ደምሴ አየለ፣ አቶ ደረሰ ዳንሱ እና ሌሎችም በሰጡት አስተያየት ለልማት ማህበሩ ዕድገት የአመራሩ ቁርጠኝነትና የህብረተሰቡን ተነሳሽነት እንደሚጠይቅ አስታውሰው የሚጠበቅባቸውን ወጥነትና ቀጣይነት ባለው ሁኔታ ድጋፍ እንደሚያደርጉ ተናግረዋል።

አክለውም ማህበሩ የተለያዩ የልማት ጥያቄዎችን የሚመልስና ለበርካቶች የሥራ ዕድል የሚፈጥር በመሆኑ የማህበሩ አባልነት እስከ ቀበሌ መዝለቅ እንደሚገባው አንስተዋል።

በመጨረሻም 11 አባላትን ያቀፈ የፕሮጀክት ቡድን ተመርጦ በጠቅላላ ጉባኤው ፀድቋል።

ዘጋቢ: ምርጫ መላኩ – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን