የጂንካ ዩኒቨርስቲ በኦሞ ወንዝ ሙላት ለተፈናቀሉ ወገኖች ድጋፍ አደረገ

ሀዋሳ፡ ነሐሴ 29/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) የጂንካ ዩኒቨርስቲ በደቡብ ኦሞ ዞን ዳሰነች ወረዳ በኦሞ ወንዝ ሙላት ለተፈናቀሉ ወገኖች ከ600 ሺህ ብር በላይ የሚገመት የተለያዩ የምግብና የአልባሳት ድጋፍ አድርጓል።

የጂንካ ዩኒቨርሲቲ ከተመሠረተበት ጊዜ አንስቶ የተለያዩ ችግር ፈቺ ተግባራትን እያከናወነ ቆይቷል፡፡ አሁን ላይ በኦሞ ወንዝ ሙላት ለተፈናቀሉ የዳሰነች ማህበረሰብ ዩኒቨርሲቲው ላደረገው ድጋፍ ምስጋና ያቀረቡት በዞኑ የዳሰነች ወረዳ ምክትል አስተዳዳሪ አቶ ዑመር ነኩዌ ናቸው።

በተከሰተው ችግር ከ5ሺህ በላይ አርብቶ አደሮች መፈናቀላቸውንም ምክትል አስተዳዳሪው ገልጸዋል።

የጂንካ ዩኒቨርስቲ ፕሬዚዳንት ጽህፈት ቤት ሀላፊ አቶ አምባ ጩፋ እንደገለፁት ዩኒቨርስቲው በተለያዩ አካባቢዎች ከሚከሰቱ ድንገተኛ አደጋዎች ሕብረተሰቡን ለመታደግ ሀላፊነቱን ሲወጣ ቆይቷል።

ዩኒቨርስቲዉ በደቡብ ኦሞ ዞን ዳሰነች ወረዳ በኦሞ ወንዝ ሙላት ምክንያት ለተፈናቀሉ ወገኖች ከ600 ሺህ ብር በላይ የሚገመት የተለያዩ የምግብና አልባሳት ቁሳቁሶችን ድጋፍ ማድረጉን ተናግረዋል።

ሀላፊው አያይዘው በወንዙ ሙላት ምክንያት በነዋሪዎች ላይ የሚከሰተውን ተደጋጋሚ ችግሮች መቅረፍ ይቻል ዘንድ ዩኒቨርሲቲዎች በተቀናጀ አግባብ በማጥናት መፍትሔ መሻት አለባቸው ብለዋል።

ዘጋበቢ፡ ዳኜ ጥላሁን – ከጂንካ ጣቢያችን