የህብረተሰቡን የልማት ፍላጎት ለማሟላት ከአንገብጋቢነት በትኩረት መሥራት እንደሚያስፈልግ የጌዴኦ ዞን አስተዳደር ጽ/ቤት አስታወቀ

አስተዳደር ጽ/ቤቱ ከሥሩ ከሚገኙ አቻ ተቋማት ጋር በ2016 በጀት ዓመት በሥራ ክንውንና 2017 በጀት ዓመት መሪ ዕቅድ የግምገማ መድረክ በዲላ ከተማ አካሂዷል፡፡

በመድረኩ የአስተዳደር ጽ/ቤቱ የልማት ዕቅድ አስተባባሪ አቶ ደምሴ ሎሌ የሥራ አፈፃፀም ሪፖርት ባቀረቡበት ወቅት በበጀት ዓመቱ በርካታ የልማትና የመልካም አስተዳደር ሥራዎች መከናወናቸውን ጠቅሰዋል፡፡

ከሁሉም ወረዳዎችና ከተማ አስተዳደሮች የቀረቡ የመልካም አስተዳደር ቅሬታዎችን ለመፍታት በተደረገው ጥረት አበረታች ውጤት መታየቱን አቶ ደምሴ በሪፖርቱ አመላክተዋል፡፡

በማህበራዊ፣ በፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ሥራዎች ትኩረት ሰጥቶ በመሥራት የህብረተሰቡን የልማትና የመልካም አስተዳደር ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ መታቀዱንም ገልፀዋል ፡፡

የዞን አስተዳደር ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ብርሃኑ ሮቤ በመሆኑ ቀልጣፋና ፈጣን የአገልግሎት አሰጣጥ ሥርዓት በመዘርጋትና በእውቀት በመምራት የህብረተሰቡን እርካታ ለማሳደግ መሥራት እንደሚያስፈልግ አሳስበዋል፡፡

የጌዴኦ ዞን አስተዳዳሪ ዋና አማካሪ አቶ ክብሩ ማሞ በበኩላቸው በግምገማ መድረኩ የሚነሱ ጠንካራ ጎኖችን በማስቀጠል በዕቅድ አፈፃፀም የተስተዋሉ ጉድለቶችን በማረም የተሻለ ከፈፀሙ መዋቅሮች ልምድና ትምህርት መውሰድ ፋይዳ ያለው መሆኑን አስረድተዋል፡፡

የህብረተሰቡን የልማት ፍላጎት ለመመለስ ከአንገብጋቢነት አንፃር ደረጃ በደረጃ መሥራት እንደሚያሰፈልግ አማካሪው ተናግረዋል፡፡

ዘጋቢ፦ እምነት ሽፈራው- ከይርጋጨፌ ጣቢያችን