የትራፊክ አደጋ ለመቀነስ ለህብረተሰቡ ግንዛቤ የማስጨበጥ ሥራ በትኩረት እየተሠራ መሆኑ ተገለፀ

ሀዋሳ፡ ነሐሴ 28/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ትራንስፖርትና መንገድ ልማት ቢሮ የ2016 በጀት ዓመት ዕቅድ አፈፃፀም እና የ2017 ዕቅድ ዙሪያ በዲላ ከተማ ውይይት መድረክ አካሂዷል።

የክልሉ ትራንስፖርትና መንገድ ልማት ቢሮ ኃላፊ ኢንጂነር ዘብዴዎስ ኤካ የውይይት መድረኩን በንግግር በከፈቱበት ወቅት የ2016 በጀት ዓመት በትራንስፖርት ዘርፍ የሚስተዋሉ ችግሮችን ለመቀነስ የመንጃ ፍቃድ አሰጣጥ ዘመናዊና በሶፍትዌር የታገዘ በማድረግ በቀድሞ ደቡብ ክልል የተጀመረውን ታርጋ የመቀየር ሥራ መጀመራቸውንም ተናግረዋል፡፡

የቢሮው ምክትልና የትራንስፖርት ዘርፍ ኃላፊ አቶ ተገኘ ግርማ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የትራፊክ አደጋ ምክንያቶችን በመለየት አደጋውን ለመቀነስ የሚረዱ ስልቶችን በመከተልና የአደጋውን አስከፊነት በአዲሱ ሥርዓተ ትምህርት እንዲካተት በማድረግ የግንዛቤ የማስጨበጥ ሥራ በትኩረት እየተሠራ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡

ሁሉንም የህብረተሰብ ክፍሎችን በማሳተፍ በዘርፉ እየታየ ያለውን አስክፊ አደጋዎችን ለመቀነስ እየተሠራ እንደሆነም ኃላፊው አስረድተዋል፡፡

በመንገዶችና ትራንስፖርት ልማት ቢሮ ምክትልና የገጠር ተደራሽ መንገድ ዘርፍ ኃላፊ አቶ መስፍን ስለሺ በዘርፉ በተከናወኑ ሥራዎች አመርቂ ውጤት መታየቱን ገልጸው በተለይም በህበረተሰብ ተሳትፎ በርካታ ሥራዎች መከናወናቸውን ተናግረዋል፡፡

በተቋሙ የሚስተዋለውን የሎጂስቲክ አቅርቦት ችግሮችን በመቅረፍ በተያዘው በጀት ዓመት የተሻለ ውጤት ለማስመዝገብ መዘጋጀታቸውንም ጠቁመዋል፡፡

የውይይቱ ተሳታፊ ማናጅመንት አባላት እና ባለሙያዎች በባለፈው በጀት ዓመት በቢሮ ደረጃ በርካታ ተግባራት መከናወናቸውን ገልጸው ለዚህም የበኩላቸውን እንደተወጡ ተናግረዋል ።

በቀጣይም በ2017 በጀት ዓመት በሁሉም ዘርፎች ቅንጅታዊ ሥርዓት በመዘርጋትና በመተጋገዝ ዕቅዱን ለማሳካት የበኩላቸውን እንደሚወጡ በመግለጽ ቢሮው አስፈላጊውን የቁሳቁስና የሎጂስቲክ አቅርቦት ችግር እንዲቀርፍላቸው ጠይቀዋል፡፡

ዘጋቢ፦ እምነት ሽፈራው- ከይርጋጨፌ ጣቢያችን