የበጀት ዓመቱን አፈፃፀም ደካማና ጠንካራ ጎኖችን በመለየት መስራት ትልቅ ፋይዳ አለው – የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ

ሀዋሳ፡ ነሐሴ 23/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) የበጀት ዓመቱን አፈፃፀም ደካማና ጠንካራ ጎኖችን በመለየት መስራት ትልቅ ፋይዳ እንደሚኖረው የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ገለፀ፡፡

የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር እና የኢንተርፕራዝና ሥራ ዕድል ፈጠራ ቢሮ ኃላፊ አቶ ገ/መስቀል ጫላ የኢንዱስትሪ ልማት ስለፈለግነው ብቻ ሳይሆን ውጤታማ በመሆን የሚመጣ መሆኑን አመላክተዋል።

መድረኩን በይፋ ያስጀመሩት የክልሉ ኢንዱስትሪ ቢሮ ኃላፊ ዶክተር እንዳልካቸው ጌታቸው በአምራች ኢንዱስትሪው ልማት ዘርፍ ተስፋ ሰጭ ሥራ እንደተሠራ ጠቁመው ከውጭ ምንዛሪ አኳያ በበጀት ዓመቱ የተሻለ ገቢ ማግኘት እንደተቻለ ጠቁመዋል።

ዘርፉ ውጤታማ እንዲሆን መሬት የማዘጋጀት ተግባር በትኩረት መሠራቱን ነው ያስረዱት።

ዘርፉን ውጤታማ ሊያደርጉ የሚችሉ ሌሎችም ተግባራት መከናወናቸውን ዶክተር እንዳልካቸው አብራርተዋል።

በዋናነትም በበጀት ዓመቱ የተከናወኑ ተግባራት ደካማና ጠንካራ ጎኖችን በመለየት የመፍትሔ አቅጣጫ ለማስቀመጥ ታስቦ መድረኩ እንደተዘጋጀ ጭምር አስረድተዋል።

የዕለቱ የክብር እንግዳ የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር እና የኢንተርፕራይዝና የሥራ ዕድል ፈጠራ ቢሮ ኃላፊ አቶ ገ/መስቀል ጫላ እንደገለጹት የኢንዱስትሪ ልማት ስለፈለግነው ብቻ ሳይሆን ውጤታማ በመሆናችን የሚመጣ ዘርፍ ነው።

ከለውጡ ማግስት ጀምሮ መንግስት ለኢንዱስትሪው ዘርፍ ትኩረት መስጠቱን የተናገሩት አቶ ገ/መስቀል ከአምራች ኢንዱስትሪ ባሻገር በግብርና፣ በማዕድን፣ በቱሪዝምና በአይቲ ዘርፍ ትኩረት የሰጠባቸው ናቸው ነው ያሉት።

ለአምራች ኢንዱስትሪው ዘርፍ መሬት ማዘጋጀት ያስፈልጋል ያሉት አቶ ገብረመስቀል፤ በኢንዱስትሪው ዘርፍ ውጤታማ ለመሆን ከሰው ኃይል አደረጃጀት ጀምሮ ማሟላት ከኢንዱስትሪው ሴክተር እንደሚጠበቅ አመላክተዋል።

በመድረኩ የ2016 ዕቅድ ክንውንና የ2017 ዕቅድ ዙሪያ ሰፊ ማብራሪያ ተሰጥቷል።

ባለድርሻ አካላቱ በዕቅድ አፈፃፀሙና በ2017 ዕቅድ ዙሪያ የተለያዩ ሀሳቦች አንስተዋል።

ዘጋቢ፡ ታምሩ በልሁ – ከአርባምንጭ ጣቢያችን