“አንድ የሴት ተማሪ የንጽህና መጠበቂያ ፓድ ለአንዲት ተማሪ” በሚል መሪ ሃሳብ የተጀመረው ንቅናቄ አበረታች ዉጤት ማምጣቱ ተገለጸ

ሀዋሳ፡ ነሐሴ 22/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) ለ2017 የትምህርት ዘመን “አንድ የሴት ተማሪ የንጽህና መጠበቂያ ፓድ ለአንዲት ተማሪ” በሚል መሪ ሃሳብ በቦንጋ ከተማ የተጀመረው ንቅናቄ አበረታች ዉጤት ማምጣቱን አስተባባሪ ወጣቶች ተናገሩ፡፡

በካፋ ዞን ቦንጋ ከተማ ለ2017 የትምህርት ዘመን በትምህርት ቁሳቁስና በንጽህና መጠበቂያ እጥረት ምክንያት አንድም ሴት ከትምህርት ገበታ እንዳትቀር አስፈላጊውን ሀብት በማሰባሰብ ላይ መሆናቸዉን ወጣት ብዙአየሁ በላቸው እና መምህርት ሩሀማ ሽፈራዉ ገልጸዋል።

በተጀመረው ንቅናቄ ማህበራዊ ሚዲያን ለበጎ ተግባር በመጠቀም በርካታ በሀገር ዉስጥና በውጭ የሚኖሩ ወገኖችን ማሳተፍ ተችሏል ነው ያሉት።

በአጭር ጊዜ ሀብት ለማሰባሰቡ በተደረገው ጥረት ከ210 ሺህ ብር በላይ ማሰባሰብ መቻሉን ገልጸዋል።

በንቅናቄው ለ500 ሴት ተማሪዎች ከ18 እስከ 24 ወራት ሊያገለግል የሚችል የንጽህና መጠበቂያ ሞዴስ የያዘ ፓድ ማዘጋጀታቸውንም ተናግረዋል።

ድጋፉ ቀጣይነትና ተደራሽነት እንዲኖረው ሁሉም አቅም በፈቀደው መጠን መረባረብ እንዳለበትም ጥሪ አቅርበዋል፡፡

የወር አበባ ሴቶች 14 አመትና ከዛም በላይ በሆነ የዕድሜ ክልል ሲደርሱ የሚያዩት ተፈጥሯዊ ሂደት መሆኑን በቦንጋ ገብረጻዲቅ ሻዎ አጠቃላይ ሆስፒታል አዋለጅ ነርሰ ስንታየሁ በለጠ ገልጸዋል።

የካፋ ዞን ሴቶች፣ ህጻናትና ማህበራዊ ጉዳይ መምሪያ ሀላፊ ወ/ሮ መዓዛ ሀይለማሪያም የወር አበባ ህብረተሰቡ በነበረው የተዛባ አመለካከት ሴቶች በተለያዩ ዘርፎች ተሳታፊና ተጠቃሚ እንዳይሆኑ እንቅፋት ሆኖ መቆየቱን ተናግረዋል፡፡

በጉዳዩ ከጊዜ ወደ ጊዜ የማህበረሰቡ ንቃተ ህሊና እያደገ መምጣቱን ጠቅሰዉ አሁንም መስራትን ይጠይቃል ብለዋል፡፡

በተለይ ሴት ተማሪዎች በትምህርታቸው ዉጤታማና ንቁ ተሳታፊ እንዲሆኑ ለማስቻል ከጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶችና አመለካከቶች ነጻ የሆነ ማህበረሰብ መፍጠር ላይ በትኩረት መሰራት አለበት ያሉት ወ/ሮ መዓዛ ወላጆች በዚህ ጉዳይ ዙርያ ከልጆቻቸዉ ጋር በግልጽ የመነጋገር ባህል ሊያዳብሩ እንደሚገባም አሳስበዋል፡፡

ዘጋቢ፡ በአሳምነው አትርሳው – ከቦንጋ ጣቢያችን