በግብርናው ዘርፍ ምርትና ምርታማነትን ወደተሻለ ደረጃ ከፍ ለማድረግ የባለሙያዎችና የባለድርሻ አካላት የተቀናጀ አሠራርን ማጠናከር እንደሚገባ ተገለጸ

ሀዋሳ፡ ነሐሴ 21/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) በግብርናው ዘርፍ ምርትና ምርታማነትን ወደተሻለ ደረጃ ከፍ ለማድረግ የባለሙያዎችና የባለድርሻ አካላት የተቀናጀ አሠራርን ማጠናከር እንደሚገባ በኣሪ ዞን የደቡብ ኣሪ ወረዳ ምክር ቤት አስታወቀ።

ወረዳው 4ኛ ዙር 6ኛ ዓመት 24ኛ መደበኛ ጉባኤውን በማካሄድ ከ330 ሚሊዮን 580 ሺህ ብር በላይ በጀት አፅድቋል።

ከዞኑ ወረዳዎች የደቡብ ኣሪ ወረዳ ካለው ምቹ የአየር ንብረት አኳያ ሁሉንም የሰብል እና የፍራፍሬ ዓይነቶች የሚመረትበት አካባቢ በመሆኑ የምክር ቤት አባለት የግብርና ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የኑሮ ዉድነትን ለማረጋጋት የሚደረገውን ጥረት ማጠናከር ይገባል ያሉት የደቡብ ኣሪ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ግዛው ሀይሌ ናቸው።

በወረዳው አንዳንድ አካባቢዎች በጥቂት ግለሰቦች ዘንድ የሚስተዋሉ የተዛቡ አመለካከትና አስተሳሰቦችን ለመቅረፍና የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ለመፍታት የሚደረገው አሰራር ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አስተዳዳሪው ተናግረዋል።

ሕብረ-ብሔራዊ አንድነት ለማጠናከር በሚደረገው ሁሉአቀፍ ጥረት ሁሉም የሕብረተሰብ ክፍሎች በብቃት መሳተፍ እንደሚገባም ተገልጿል ።

ከማህበራዊ ዘርፎች የትምህርት ስብራትን ለመጠገን በየደረጃዉ የተጀመሩ ተግባራትን በቅንጅት በመፈፀም የተሻለ ዉጤት ለማምጣት መጣር እንደሚያስፈልግ የደቡብ ኣሪ ወረዳ ምክር ቤት ዋና አፈጉባኤ አቶ ስምኦን ኦሺ ገልጸዋል።

በመልካም አስተዳደር፣ የዋጋ ንረትን ለማረጋጋት፣ የጤና ልማትና በፍትህ ስርዓት አፈፃፀም ዙሪያ የሚታዩ ተግዳሮቶችን መሻገር የሚያስችሉ ተግባራትን በመለየት የምክር ቤቱ አባላት መክረዋል።

በገቢ ግብር አሰባሰብ ሂደት የሚስተዋሉ ችግሮችን በመፍታት የተጀመሩ መሠረተ ልማት በተደራጀ አግባብ በማጠናቀቅ ለሕብረተሰቡ ተገቢውን አገልግሎት እንዲሰጥ መሥራት እንደሚገባም ተገልጿል።

ጉባኤው ለ2017 ዓ.ም ሥራ ማስኬጃና ደመወዝ ከ330 ሚሊዮን 580 ሺህ ብር በጀትና የተለያዩ ፅህፈት ቤት ሀላፊዎችን ሹመት በማፅደቅ ተጠናቋል።

ዘጋቢ፡ ዳኜ ጥላሁን – ከጂንካ ቅርንጫፍ