56 ሺህ በላይ ተማሪዎችን ለመቀበል በምዝገባ ሂደት ላይ መሆኑን የኮሬ ዞን ትምህርት መምሪያ ገለጸ

ሀዋሳ፡ ነሐሴ 20/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) በ2017 የትምህርት ዘመን 56 ሺህ በላይ ተማሪዎችን ለመቀበል አቅዶ በምዝገባ ሂደት ላይ መሆኑን የኮሬ ዞን ትምህርት መምሪያ አስታወቀ።

የኮሬ ዞን ትምህርት መምሪያ ኃላፊ አቶ ታደለ አሸናፊ እንደገለጹት በ2017 የትምህርት ዘመን ቅድመ መደበኛና ጎልማሳን ጨምሮ 56 ሺህ 361 ተማሪዎችን ለመቀበል አቅዶ ምዝገባ እያካሄዱ መሆኑን ተናግረዋል።

በዞኑ 83 መደበኛ ትምህርት ቤቶች እንደሚገኙና በሁሉም አከባቢዎች ምዝገባ እየተካሄደ መሆኑን የተናገሩት አቶ ታደለ የመማር ማስተማር ተግባር በተያዘው የጊዜ ሰሌዳ ተግባራዊ እንዲሆንና የተጀመረው የተማሪዎች ምዝገባና የዝግጅት ምዕራፍ ከወዲሁ መጠናቀቅ ይገባዋል ብለዋል።

በዞኑ የዶንሶ 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት መምህርና የተማሪዎች ምዝገባ ፈፃሚ መምህር መስፍን ብርሀኑ ለምዝገባ የተፈቀደው ጊዜ ረጅም በመሆኑ በቀን ውስጥ የሚመዘገቡ ተማሪዎች ቁጥር ከወትሮው ዝቅተኛ እንደሆነ ነው የገለጹት።

በኬሌ ሙሉ 1ኛ ደረጃ እና ዶንሶ 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ሲመዘገቡ አግኝተን ካነጋግረናቸው ተማሪዎች ቤዛዊት እንግዳየሁ እና ግሩም አወቀ የተማሪዎች በጊዜ መመዝገብ በወላጆች የትምህርት ቁሳቁስ መሟላትና የትምህርት ቤቶች ዝግጅት ለትምህርት ሥራ ወሳኝ ነው ብለዋል፤ ዕለቱን በጉጉት እንደሚጠብቁ በመግለጽ።

ዘጋቢ: ምርጫ መላኩ – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን