በኢንቨስትመንት መስክ ለሚሰማሩ አልሚዎች የተጠናከረ ድጋፍ እንደሚያደርግ የጌዴኦ ዞን አስተዳደር አስታወቀ

በዞኑ ይርጋጨፌ 1 መቶ 7 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ ለጠቅላላ አገልግሎት የሚውል ህንጻ ተገንብቶ ተመርቋል።

በይርጋጨፌ ከተማ ለጠቅላላ አገልግሎት የሚውል ህንጻ ያስገነባው ወጣቱ ባለሀብት አብዮት አገዘ 1መቶ 7 ሚሊዮን ብር ወጪ ማድረጉን ተናግሯል።

ብዙነሽና አገዘ ህንጻ የሚል ስያሜ የተሰጠው ህንጻ አንድ ዓመት ከስድስት ወር በሆነ ጊዜ ገንብቶ ማጠናቀቁን የገለጸው ወጣቱ ባለሀብት ለባንክ፣ ለድርጅት፣ ለሱቆችና ለአልጋ አገልግሎት የሚውል መሆኑን ተናግሯል።

ህንጻው ከግንባታው ጀምሮ ባለው ለቋሚና ጊዜያዊ ሠራተኞች የሥራ ዕድል መፍጠሩን የገለጸው ወጣት አብዮት በዋነኝነት በዙሪያው ካሉ አርሶአደሮች ጀምሮ የተለያየ የህብረተሰብ ክፍልን አመስግኗል።

የተለያዩ የኢንቨስትመንት ሥራዎችን በከተማው ለመሥራት ከመብራት ኃይል ጋር ተያይዞ ያለ የቢሮክራሲ ጉዳይ እንዲቀረፍም ባለሀብት ጠይቋል።

በከተማው በአሁኑ ሰዓት እየተነቃቃ የመጣው የኢንቨስትመንት ሥራ ሌሎችም በዘርፉ እንዲሰማሩ የሚያደርግ ነው ያሉት የከተማ አስተዳደሩ ከንቲባ አቶ ታደለ ጥላሁን ሌሎችም በዘርፉ መሰማራት ለሚፈልጉ አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርጉ ተናግረዋል።

የ96 ዓመት ዕድሜ ያላት ከተማዋ በርካታ የኢኮኖሚ አውታሮች ያሏት ቢሆንም ማደግና መለወጥ ያለባትን ያህል አላደገችም ያሉት ከንቲባው፤ መካን መስላ የነበረችውን ከተማ ልጆቿ ተቀራርበው በመሥራት እያስዋቧት ይገኛሉ ብለዋል።

በከተማዋ በ3 ዓመት ጊዜ ውስጥ ከ30 በላይ ህንጻዎች ተገንብተው ወደሥራ እንደገቡ የተናገሩት ከንቲባው የከተማዋን ኢኮኖሚ ለማሳለጥ ደረጃቸውን የጠበቁ ህንጻዎች ግንባታ በየአካባቢው የጀመሩና በሂደት ላይ ያሉ ባለሀብቶች በርትተው እንዲሰሩ ጥሪ አቅርበዋል።

ይርጋጨፌ ምዕራባዊያኑ የሚያውቋትን ያህል ውስጧ ሲታይ ያለው እውነታ እጅግ የተለያየ ነው ያሉት የጌዴኦ ዞን አስተዳዳሪ ዶ/ር ዝናቡ ወልዴ፤ በዚህም በቁጭት ተነስተው ስሟን ለማደስ የሚሰሩ ወጣቶች ሊበረታቱ ይገባል ብለዋል።

ባለሀብቱ ሊያለማና ሊሠራ ሲመጣ መላው የዞኑ አመራሮች እጃቸውንና ህሊናቸውን አንጽተው ሊቀበሏቸው እንደሚገባ ዶክተር ዝናቡ አሳስበዋል።

በከተማው በኢንቨስተመንት መስክ ከተሰማሩ ባሀብቶች መካከል አቶ ሰይድ አሊና አቶ ቁምላቸው ቢሻው በዘርፉ ያለው መነቃቃት ብርታት ሆኗቸው ወደ ልማት ገብተው በዘርፉ መሰማራታቸውን ተናግረዋል።

ዘጋቢ: ውብሸት ካሳሁን – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን