የኦሞ ወንዝና የቱርካና (ሩደልፍ) ሐይቅ በየቀኑ እየተስፋፋ በኦሞራቴ ከተማና አካባቢው ላይ የሚፈጥረው ስጋት እየጨመረ መምጣቱን በአካባቢው ላይ የመከላከል ሥራውን እያከናወነ ያለው ግብረሀይል አስታወቀ

ግብረሀይሉ ወንዙ ሞልቶ ጉዳት እንዳያስከትል የመከላከል ሥራው በየአቅጣጫው እየተካሄደ መሆኑን የገለፁት የዳሰነች ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ታደለ ሀቴ ናቸው።

ውሃው በየአቅጣጫው ሞልቶ እየተስፋፋ ያለውን በማሽነሪ የመከተርና አፈር የመቆለል(ካብ) ተግባር እየተሰራ እንደሚገኝ ዋና አስተዳዳሪው አስረድተዋል።

ለአካባቢው ማህብረሰብ ግንዛቤ የማስጨበት ሥራ እየተሠራና ውሃው ከሚደርስበት አካባቢ የማስወጣት ተግባር ለማከናወን እየተሠራ እንዳለም አቶ ታደለ ተናግረዋል።

በአካባቢው በመስኖ የለሙ መሬቶች ጉዳት እየደረሰባቸው እንደሚገኝ ዋና አስተዳዳሪው ጠቅሰው ከዚህ በፊት ወንዙ ሞልቶ በተለያዩ ቦታዎች የተጠለሉ ማህበረሰብ አካላት ላይ ዳግም የመፈናቀል ስጋት መፈጠሩንም አስረድተዋል።

ውሃው ከሚያሳየው ባህሪ አንፃር ለመከላከሉ ሥራ በአካባቢው የሚገኙ ማሽነሪዎች በቂ ባለመሆናቸው ተጨማሪ ማሽነሪዎች እንደሚያስፈልጉ ተገልጿል።

የመከላከል ሥራው በሁሉም በኩል ተጨማሪ ማሽነሪዎችን በማስመጣት ተግባራዊ ለማድረግ እየተሠራ እንደሆነ የደቡብ ኦሞ ዞን ግብርና መምሪያ ሀላፊ አቶ ባንኬ ሱሜ ገልፀዋል።

በግብረ ሀይሉ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል መስኖና ቆላማ አካባቢ ምክትል ቢሮ ሀላፊ አቶ አይዴ ሎሞዶን ጨምሮ የደቡብ ኦሞ ዞን የዳሰነች ወረዳ አመራር አካላት ጉዳዩን በማስመልከት በመወያየት መፍትሔ አቅጣጫ ዙሪያ የጋራ መግባባት ላይ በመድረስ የመከላከል ሥራው ላይ ርብርብ እንደሚደረግ ተብራርቷል።

ዘጋቢ: ተመስገን አበራ – ከጂንካ ቅርንጫፍ