በጠምባሮ ልዩ ወረዳ በሆዶ ቡልቱማ ቀበሌ እንደ ሀገር የተያዘው በአንድ ጀምበር ችግኝ ተከላ መርሃ-ግብር ተካሂዷል

ሀዋሳ፡ ነሐሴ 17/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ጠምባሮ ልዩ ወረዳ እንደ ሀገር የተያዘው በአንድ ጀምበር የ600 ሚሊየን ችግኝ ተከላ መርሃ-ግብር በሆዶ ቡልቱማ ቀበሌ ተካሂዷል፡፡

በአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብሩ ላይ ተገኝተው ንግግር ያዳረጉት የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ቴክኒክና ሙያ ትምህርትና ሥልጠና ቢሮ ኃላፊ አቶ አሰፋ ዲቼ፤ የአረንጓዴ አሻራ ልማት ፕሮጀክት ከኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊ፣ ፖለትካዊ እና ስነ-ምህዳራዊ ጠቃሜታው በሻገር በዓመቱ  ያቀድነውን የአረንጓዴ ልማት  ግብ ማሳካትን የሚያሳይ  ታላቅ ሀገራዊ ፕሮጀክት ነው ብለዋል።

ባለፉት ዓመታት በተከናወኑ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ሥራዎች ዘርፈ ብዙ ኢኮኖሚያዊና ስነ-ምህዳራዊ ጠቃሜታዎች ተገኝተዋል ያሉት ኃላፊው እየተሰራ ባለው የአረንጓዴ አሻራ ልማት ዛፍን ከመትከል በሻገር ለምግብነት የሚውሉ የአትክልትና የፍራፍሬ ችግኞችን በማልማት  በምግብ ዋስትና እራሳችንን ለማስቻል ያለው አስተዋጽኦ የጎላ መሆኑንም ተናግረዋል።

አክለውም ችግኝ መትከል ብቻ ሰይሆን ለተተከሉ ችግኞች ተገቢውን ጥበቃና እንክብካቤ በማድረግ በታቀደው ልክ ውጤታማ መሆን እንዲቻል ሁሉም የህብረተሰብ ክፍል የድርሻውን እንዲወጣም አሳስበዋል።

በአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብሩ ላይ የኢፌዲሪ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባልና በምክር ቤቱ የጤና፣ ማህበራዊ፣ ባህልና ስፖርት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ ዶክተር ታደለ ቡራቃና የክልል ምክር ቤት አባል ወ/ሮ አሰለፈች ኃይሌን ጨምሮ የሙዱላ ከተማ አስተዳደርና የልዩ ወረዳ አመራሮች  እንዲሁም ህብረተሰቡ በነቂስ ወጥተው ተሳትፈዋል።

የጠምባሮ ልዩ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ ኢንጂነር ሀብታሙ በላይነህ በበኩላቸው እንደ ሀገር በአንድ ጀምበር 600 ሚሊዮን ችግኝ ተከላ አካል የሆነውን የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ለማሳካት  በልዩ ወረዳው  በርካታ ተግባራት መከናወናቸውን ገልጸዋል።

ይህ የአረንጓዴ አሻራ ልማት ሥራ  የአየር ንብረት ለውጥን ከመከላከል በሻገር ዘርፈ ብዙ ጠቃሜታዎች ስላሉት ህብረተሰቡ አስፈላጊውን እንክብካቤና ጥበቃ እንዲያደርግ በትኩረት ይሰራል ብለዋል።

በችግኝ ተከላው መርሃ-ግብሩ በትምህርት ተቋማት እንዲሁም በሃይማኖት ተቋማት የምግብ ዋስትናን የሚያረጋግጡ ችግኞች የተተከሉበት ሲሆን የቀጣይ ሀገር ባለቤት የሆኑ ህፃናትም በተከላ መርሃ-ግብሩ ተሳታፊዎች ሆነዋል።

ዘጋቢ: ሙሉነሽ ለማ – ከሆሳዕና ጣቢያችን