በኮሬ ዞን የአንድ ጀንበር ችግኝ ተከላ መርሐ ግብር እየተካሄደ ነው

የችግኝ ተከላ ፕሮግራሙን በንግግር የከፈቱት የኮሬ ዞን ምክትል አስተዳዳሪና የግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ አስታረቀኝ አንደባ በሀገር ደረጃ በአንድ ጀንበር ችግኝ ተከላ መርሐ ግብር ከዞኑ በተለዩ 8 ማዕከላት የተለያዩ የችግኝ ዓይነቶች መተከላቸውን ገልጸዋል።

አክለውም የሚተከሉ ችግኞች የአየር መዛባትና የአፈር መሸርሸር ከመከላከል ባሻገር ምርትና ምርታማነትን በመሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ስላለው አንድ ቀን መትከል ብቻ ሳይሆን ቀጣይነት ያለው ተግባር መሆኑንም አስረድተዋል።

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ኢንዱስትሪ ቢሮ ኃላፊ ዶክተር እንዳልካቸው ጌታቸው በመርሐ ግብሩ ላይ ተገኝተው ባስተላለፉት መልዕክት ችግኝ ተከላ እንደ ሀገር ታሪክ የምንተክልበትና ትውልድን የምናፀናበት በመሆኑ ቀጣይነት ባለው ሁኔታ አንድ ሆንን የብልጽግናን ራዕይን እናሳካለን ብለዋል።

ከአካባቢ አባቶች አቶ ኃይሌ ሉታ ጠብቀው ያቆዩት ቅርሶችና ዛሬ ላይ እየተተከሉ ያሉ ችግኞችን ወጣቱ ትውልድ በመንከባከብ በዘላቂነት አንዲያቆይ አደራ አስተላልፈዋል።

ከመርሐ ግብሩ ተሳታፊዎች መካከል ወ/ሮ ታመነች ታሪኩና ሌሎች የችግኝ ተከላ ፕሮግራም ለአከባቢው ያለውን ጠቀሜታ በመገንዘብ አሻራቸውን ማሳረፋቸውን ተናግረዋል።

ዘጋቢ: ምርጫ መላኩ – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን