የዛሬው ሀገር አቀፍ የችግኝ ተከላ ዘመቻ ኢትዮጵያ አዲስ አለም አቀፍ ክብረ ወሰን የምታስመዘግብበት ነው – አቶ እንዳሻው ጣሰው

ሀዋሳ፡ ነሐሴ 17/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) የዛሬው ሀገር አቀፍ የችግኝ ተከላ ዘመቻ ኢትዮጵያ አዲስ አለም አቀፍ ክብረ ወሰን የምታስመዘግብበት ነው ሲሉ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ እንዳሻው ጣሰው ገለጹ፡፡

የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል አረንጓዴ አሻራ ማስጀመሪያ መርሃ ግብር በስልጤ ሳንኩራ ወረዳ በረግዲና ቆሬ ቀበሌ በይፋ ተጀምሯል።

ስነ ስርዓቱን በንግግር የከፈቱት የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ እንዳሻው ጣሰው ባሰሙት ንግግር ኢትዮጵያ በአንድ ጀምበር 600 ሚሊየን ችግኞችን በመትከል የአለም ክብረወሰንን በእጇ ታስገባለች ብለዋል።

የአረንጓዴ አሻራና የአከባቢ ጥበቃ ስራ የሀገሪቱን የብልፅግና ጉዞ ለማረጋገጥ፣ ከራሷም አልፎ የሌሎች ሀገራትን ስነ ምህዳር ሚዛን ለመጠበቅ አውንታዊ ሚና አለው ብለዋል።

የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ፣ ኢትዮጵያን በአለም አቀፍ መድረክ በአዎንታዊ ጎን ከፍ ለማድረግ፣ ገንቢ የጋራ ትርክትን ለመፍጠር ፍቅርና አንድነትን ለማጎልበት ፋይዳው የጎላ ስለመሆኑም አመላክተዋል።

ኢትዮጵያ በአንድ አመት 7 ነጥብ 5 ቢሊዮን ችግኝ መትከሏ ከአለም ህዝብ ቁጥር ጋር ተቀራራቢ መሆንን የጠቆሙት ርዕሰ መስተዳድሩ፥  በአንድ ጀምበር የሚተከለው 600 ሚሊዮን ችግኝ ከአፍሪካ ህዝብ ግማሽ ቁጥር ጋር ተቀራራቢ መሆኑ ለየት ያደርገዋል ብለዋል።

ለዘመቻው መሳካታ የበኩላቸውን ለተወጡ አካላትም ርዕሰ መስተዳድሩ ምስጋና አቅርበዋል ።

በስነ-ስርዓቱ ላይ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ እንዳሻው ጣሰው፣ የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር፣ የማህበራዊ ክላስተር አስተባባሪና የትምህርት ቢሮ ኃላፊ አቶ አንተነህ ፈቃዱ፣ የክልሉ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ ወ/ሮ ፋጤ ስርሞሎ፣ የክልሉ መንግሥት ዋና ተጠሪ ዶክተር ዲላሞ ኦቶሬ፣ እና ሌሎች ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች እንዲሁም በርካታ በስልጤ ዞን የሳንኩራ ወረዳ ነዋሪዎች ተገኝተዋል።

ዘጋቢ፡ ጀማል የሱፍ