በአንድ ጀንበር ለሚተከለው የችግኝ ተከላ አስፈላገውን ዝግጅት ማጠናቀቃቸውን የማጂ እና የመኢኒት ሻሻ ወረዳዎች ገለጹ

ሀዋሳ፡ ነሐሴ16/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) በነገው እለት በአንድ ጀንበር ለሚተከለው የችግኝ ተከላ ዘመቻ አስፈላገውን ዝግጅት ማጠናቀቃቸውን በምእራብ ኦሞ ዞን የማጂ እና የመኢኒት ሻሻ ወረዳዎች ገለጹ።

የአረንጓዴው አሻራ መረሀግብር አንዱ አካል የሆነው እና እንደ ሀገር 600 ሚሊየን ችግኝ ለመትከል የተያዘውን እቅድ ለማሳካት በሁሉም አከባቢዎች ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን የገለጹት የወረዳው ግብርናና አከባቢ ጥበቃ ህብረት ስራ ጽህፈት ቤት ሀላፊው አቶ አበበ ባቡ የተናገሩት።

እንደ እርሳቸው ገለጻ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸው የተለያዩ የደን እና የፍራፍሬ ችግኞች ለተከላ መዘጋጀታቸውን ጠቁመው፥ ለተከላውም እስካሁን 429 ሺ ጉድጓዶች በተለዩ 14 የተከላ ቦታዎች  መዘጋጀታቸውን ጠቁመዋል።

በዚህም ከ2 ሺ በላይ የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች እንደሚሳተፉም ተናግረዋል።

በተመሳሳይ በዞኑ በመኢኒት ሻሻ ወረዳ የተለያዩ የደን እና ፍራፍሬ ችግኞችን ለመትከል አስፈላጊውን ዝግጅት ማጠናቀቁን የወረዳው ግብርና አከባቢ ጥበቃ ህብረት ስራ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ አየለ ዱርኩባ ተናግረዋል።

ችግኙም በተለዩ 15 ቦታዎች በ160 ሄክታር ላይ እንደሚተከል ገልጸው በተከላው በወረዳው የሚገኙ ከ20 ሺ የሚበልጡ የህብረተሰብ ክፍሎች ተሳታፊ እንደሚሆኑ ተናግረዋል።

ዘጋቢ: አብዮት በቀለ – ከሚዛን ጣቢያችን