ሀዋሳ፡ ነሐሴ 15/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) በተጠናቀቀው 2016 በጀት አመት 302 የትራፊክ አደጋዎች መከሰታቸውን የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ትራንስፖርትና መንገድ ልማት ቢሮ አስታወቀ፡፡
በክልሉ ካሉ 22 የአሽከርካሪ ማሰልጠኛ ተቋማት መካከል 15ቱ ከደረጃ በታች በመሆናቸው እርምጃ መውሰዱንም ቢሮው አስታውቋል፡፡
በተጠናቀቀው 2016 በጀት አመት 302 የትራፊክ አደጋዎች የተከሰቱ ሲሆን 611 ሰዎች ላይ ቀላልና ከባድ ጉዳት ሲደርስ 71 ሰዎች ደግሞ ለሞት መዳረጋቸውን የክልሉ ትራንስፖርትና መንገድ ልማት ቢሮ ምክትል ሃላፊና የትራንስፖርት ዘርፍ ሃላፊው አቶ አሸብር ኢካሎ ተናግረዋል።
በየጊዜው ለሚከሰቱ የትራፊክ አደጋዎች መንስኤ ከሆኑ ጉዳዮች መካከል የአሽከርካሪዎች ብቃት ማነስና ህጋዊነት ተጠቃሽ ምክንያት ናቸው ብለዋል።
በክልሉ 22 የአሽከርካሪ ማሰልጠኛ ተቋማት ያሉ ሲሆን ከእነዚህም 15 የሚሆኑት መስፈርቶችን ያላሟሉና ከደረጃ በታች በመሆናቸው ለ4 ወራት እገዳ ተጥሎባቸዋል ነው ያሉት።
በደረሰው የትራፊክ አደጋ ከ14 ሚሊዮን ብር በላይ የንብረት ውድመት ማስከተሉን የተናገሩት አቶ አሸብር 77 የሚደርሱት አደጋዎች የደረሱት ያለመንጃ ፍቃድ ሲያሽከረክሩ በነበሩ አሽከርካሪዎች መሆኑን ገልጸዋል።
በፍጥነት ማሽከርከር፣ ለእግረኛ ቅድሚያ ያለመስጠትና ያለመንጃ ፍቃድ ማሽከርከር ዋነኛ የትራፊክ አደጋዎች ምክንያት መሆናቸውን አቶ አሸብር ጠቁመዋል።
በተለይ በአሽከርካሪ ማስልጠኛ ተቋማት ያሉ ህገወጥ አሰራሮችን ለማረም በሚደረገው ጥረት በየደረጃው የሚገኙ የዘርፉ አመራሮችና ሃላፊዎች የድርሻቸውን መወጣት እንዳለባቸው አሳስበዋል።
ዘጋቢ፡ ጦያር ይማም – ከሚዛን ጣቢያችን
More Stories
የምክር ቤቶችን አቅም በማጎልበት የህዝብ ተጠቃሚነትን ማጎልበት ይገባል ሲሉ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልላዊ መንግስት ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ አቶ አለማየሁ ባውዲ ተናገሩ
ማህበራዊ ሚዲያን ለበጎ አላማ በማዋልና ገዢ ትርክትን በማስረጽ የቱሪስት መዳረሻዎችን ማስተዋወቅ እንደሚገባ ተገለጸ
በምግብ ሰብል ራስን የመቻል አቅም ማሳደግ ላይ በልዩ ትኩረት እየተሰራ መሆኑ ተገለጸ