ሀምሌ 17 ቀን 2016 ዓመተ ምህረት በሚከናወነው የአንድ ጀንበር ችግኝ ተከላ ሴቶች በንቃት እንደሚሳተፉ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልላዊ መንግስት ሴቶች ሊግ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት አስታወቀ

በክልል ደረጃ ከሚተከሉ ችግኞች 9 ነጥብ 4 ሚሊዮን የሚሆነው በሴቶች የሚሸፈን መሆኑን የሴቶች ሊግ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ሀላፊ ወ/ሮ ሰብለጸጋ አየለ ተናግረዋል።

በኢትዮጵያ ከ2 ሺ 11 ዓ.ም ጀምሮ ተግባራዊ ሲደረግ የቆየው የአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር በሀገሪቱ የነበረውን የደን ሽፋን ከማሳደጉም በላይ በአየር ንብረት ለውጥ ላይ ተጨባጭ ዉጤት ማምጣቱንም ተናግረዋል።

በመርሃ-ግብሩም ሴቶች ከፍተኛውን ድርሻ እየተወጡ መሆናቸውን የገለጹት ኃላፊዋ ለዘመቻው መሳካት በየደረጃው የሚገኙ አካላት የበኩላቸዉን አስተዋጽኦ ማበርከታቸውን አስታውሰዋል።

የ2016 የአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር አካል ለሆነው የ600 ሚልዮን የአንድ ጀንበር ችግኝ ተከላ እንደ ሀገር አስፈላጊዉ ቅድመ ዝግጅት ሥራዎች ተጠናቀዋል።

ከዚህም የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል 18 ነጥብ 9 ሚሊየን ጥምር የደን ችግኞችን ለመትከል መዘጋጀቱን ከክልሉ ግብርና ቢሮ ያገኘነዉ መረጃ ያመለክታል።

በመሆኑም ሀምሌ 17 ቀን 2016 ዓመተ ምህረት በሚከናወነው የአንድ ጀንበር ችግኝ ተከላ የክልሉ ሴቶች በንቃት እንዲሳተፉ ለማድረግ አስፈላጊው ቅድመ ዝግጅት መደረጉንም ወ/ሮ ሰብለጸጋ ገልጸዋል።

በክልሉ ሁሉም አካባቢዎች ለተከላ በተለዩ 813 ቦታዎች ከሚተከለው 18 ነጥብ 9 ችግኞች መካከል 9 ነጥብ 4 ያህሉ በሴቶች የሚከናወን ይሆናል ብለዋል።

ዘጋቢ፡ አሳምነዉ አትርሳዉ – ከቦንጋ ጣቢያችን