ነሐሴ 17/2016 ዓ.ም ለሚከናወነዉ የአንድ ጀምበር የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር 5 ሚሊዮን 2 መቶ 55 ሺ ችግኞችን ለመትከል ቅድመ ዝግጅት መጠናቀቁን የካፋ ዞን ግብርና፣ አካባቢ ጥበቃና ህብረት ስራ ልማት መምሪያ አስታወቀ
መምሪያዉ ዞናዊ መርሃ ግብሩን በጊምቦ ወረዳ ጎጀብ ቀበሌ ላይ የሚያስጀምር መሆኑን አስታውቋል።
የመምሪያዉ ምክትል ሃላፊና የተፈጥሮ ሃብትና አካባቢ ጥበቃ ዘርፍ ሃላፊ አቶ ተረፈ ወልደገብርኤል ለደቡብ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ድርጅት ቦንጋ ጣቢያችን እንደገለጹት በዞኑ በሚገኙት 12 ወረዳዎችና 5 ከተማ አስተዳደሮች በተለዩ 2መቶ 98 የችግኝ መትከያ ቦታዎች ላይ የተከላ መርሃ ግብር እንደሚከናወን ገልጸዋል።
ይህም በሄክታር ሲሰላ ወደ 2ሺ 1መቶ ሄክታር እንደሚጠጋ የገለጹት አቶ ተረፈ፤ በተከላዉም በዞኑ የሚገኙ ከ3መቶ ሺ በላይ የህብረተሰብ ክፍሎች እንደሚካፈሉ ተናግረዋል።
የመሬት ለምነትን የሚያስጠብቁ እና ለእንስሳት መኖ የሚሆኑ እንዲሁም እንደ አቮካዶ፣ ሙዝና መሰል ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸዉ ችግኞች 60 በመቶ ያህሉን እንደሚሸፍኑ ገልጸዋል።
በእለቱ ዞናዊ የአንድ ጀምበር የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር በጊምቦ ወረዳ ጎጀብ ቀበሌ የሚከናወን ሲሆን 46 ሄክታር መሬት ላይ 1መቶ ሺ ችግኝ በማዘጋጀት ለተካላ ቅድመ ዝግጅት መጠናቀቁን ተናግረዋል።
ለዚህም 5 ሺህ ያህል የወረዳዉ ነዋሪዎች የሚሳተፉ ሲሆን የፌደራል፣ የክልል፣ የዞንና የወረዳዉ የስራ ሃላፊዎች እንዲሁም የሚመለከታቸዉ አካላት ይገኛሉ ተብሎ ይጠበቃል።
ዘጋቢ፡ ትዕግስቱ ጴጥሮስ – ከቦንጋ ጣቢያችን

More Stories
የአስተሳሰብና የተግባር አንድነት በማጠናከር ክልላዊ አንድነትን ማጎልበት እንደሚገባ ተገለጸ
ህዝበ ሙስሊሙ የመውሊድ በዓልን ሲያከብር በብዝሃነት ውስጥ የሚንፀባረቁ የመረዳዳትና የአብሮነት በጎ እሴቶችን ይበልጥ በማጠናከር ሊሆን እንደሚገባ ተገለጸ
የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ብልፅግና ፓርቲ ኃላፊና የየዞን ከፍተኛ አመራሮች በሣውላ ማረሚያ ተቋም አረንጓዴ አሻራቸውን በማኖር ልዩ ልዩ የልማት ሥራዎችን ጎበኙ