የደብረታቦር በዓል በሆሳዕና ከተማ በድምቀት ተከበረ
ሀዋሳ፡ ነሐሴ 13/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) የደብረታቦር በዓል ሃይማኖታዊ ይዘቱን በጠበቀ መልኩ በሆሳዕና ደብረ -ምህረት ወደብረ-ታቦር ቅዱስ በዓለ-ወልድ ወቅዱስ ገብርኤል ቤተክርስቲያን በደማቅ ሁኔታ ተከብሮ ውሏል።
የሆሳዕና ደብረ ምህረት ወደብረታቦር ቅዱስ በዓለወልድ ወቅዱስ ገብርኤል ቤ/ያን አስተዳዳሪ መላከ ሰላም ቀሲስ ተዘራ ከበደ እና በሀዲያ ስልጤ ሀገረ ስብከት የሆሳዕና ካህናት ማሰልጠኛ ተቋም ርዕሰ መምህርና የሆሳዕና ደብረ ፀሐይ አቡነ ተክለሀይማኖት ቤ/ያን አስተዳዳሪ መጋቤ ሰናያት ቀሲስ ፍስሐ ሀብተወልድ የደብረ ታቦር በዓል ኢየሱስ ክርስቶስ ሶስቱን ደቀ መዛሙርት ይዞ ወደ ደብረ ታቦር ተራራ በመውጣት ግርማ መለኮቱን የገለጠበትን አብነት በማድረግ የሚከበር ታላቅ በዓል መሆኑን ገልፀዋል።
የደብረ ታቦር በዓል በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤ/ያን ከሚከበሩ ከ9ኙ አበይት በዓላት መካከል አንዱ መሆኑንም ተናግረዋል።
ደብረ ታቦር ቃሉ የግዕዝ ሲሆን ትርጉሙም የታቦር ተራራ ነው፡፡ በኢየሩሳሌም ናዝሬት አካባቢ በሰማሪያ አውራጃ የሚገኝ ተራራ ነው ያሉት አባቶቹ ኢየሱስ ክርስቶስ ሶስቱን ደቀ መዛሙርት፥ ጴጥሮስን ያዕቆብንና ዮሐንስን ይዞ ወደ ተራራው በመውጣት ግርማ መለኮቱን የገለጠበትን አቢነት በማድረግ የሚከበር ታላቅ በዓል ነው ብለዋል።
በዓሉ ሲከበር በተራራው ላይ የተከሰተው ታላቅ ነጎድጓድ ምሳሌ ጅራፍ ማጮህ፣ ለተገለጠው ብርሃነ መለኮት ምሳሌ ችቦ ማብራትና እንዲሁም በወቅቱ ተዓምራት ተመስጠው በቦታው ላረፈዱ እረኞች ቤተሰቦቻቸው ለመብያ የሚሆን ምግብ ምሳሌ ሙልሙል ማዘጋጀት በበዓሉ ወቅት የሚከወኑ ሃይማኖታዊ ትውፊቶች መሆናቸውን ተናግረዋል።
ወቅቱ በሃይማኖቱ አስተምህሮ የክረምት ማብቅያ፣ ከጉምና ጭጋግ መላቀቂያ ወደ አዲሱ የፀደይ ዘመን መሻገሪያ መሆኑን አብራርተዋል፡፡
ዘጋቢ:-አማኑኤል አጤቦ- ከሆሳዕና ጣቢያችን

More Stories
የአፍላ ወጣቶችና ወጣቶችን የስነ ተዋልዶ ጤና ችግሮች ለመቅረፍ የተጀመሩ ጥረቶችን ለማጎልበት የጤና አደረጃጀቶችን ሚና ማሳደግ እንደሚገባ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ አስታወቀ
ወደ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የመግባት ዕድል ያገኙ ተማሪዎች የበለጠ ውጤታማ ለመሆን ትምህርታቸው ላይ ብቻ ሊያተኩሩ እንደሚገባ መልዕክት ተላለፈ
የሀዲያ ዞን ፋይናንስ መምሪያ ለ2018 በጀት ዓመት ከ10 ቢልዮን ብር በላይ በጀት ለተለያዩ የልማት ስራዎች እንዲውል በተገቢው እንደሚሠራ ገለፀ